የቻይናው ግዙፍ ኩባንያ ኃጅዬን ግሩፕ በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገነባው ኢንዱስትሪ ፓርክ ቦታ ላይ የተነሱ አርሶ አደሮች፣ ሊሰጣቸው የታቀደው ተለዋጭ ቦታ ለኑሮ ምቹ ባለመሆኑ እንደማይረከቡት አስታወቁ፡፡
አርሶ አደሮቹ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 ውስጥ በሚገኘው ማንጎ በተባለ አካባቢ በነፍስ ወከፍ 250 ካሬ ሜትር ቦታ እንደሚሰጣቸው ተገልጾላቸዋል፡፡ ነገር ግን ይህ ቦታ የወንዝ ዳርና ገደላ ገደል ከመሆኑም በላይ ተፋሰሱ የተበከለ በመሆኑ፣ ለኑሮ ፍጹም የማይመች ነው በማለት እንደማይረከቡ አስታውቀዋል፡፡
በአካባቢው የሚገኘው የአቃቂ ወንዝ የኢንዱስትሪ ብክለት ያጠቃው ከመሆኑም በተጨማሪ፣ አርሶ አደሮቹ ሊሰጣቸው ከታሰበው ቦታ በላይ በኩል የአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን የከተማውን የፍሳሽ ቆሻሻ የሚያጣራበት ጣቢያ ይገኛል፡፡
የኃጅዬን ኢንዱስትሪ ፓርክ ተነሺዎች ያቋቋሙት ኮሚቴ አባል አቶ መንገሻ ብርሃኑ፣ ‹‹ሊሰጥ የሚገባው ቦታ ከተነሳንበት አንድ ኪሎ ሜትር ዙሪያ ውስጥ መሆን አለበት፡፡ ነገር ግን ሊሰጠን የታቀደው ከአሥር ኪሎ ሜትር ዙሪያ ውጭ ነው፡፡ ይህም ከማኅበራዊ ሕይወታችን ያራርቀናል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹የሚሰጠን ቦታ በመሠረተ ልማት የተሟላ መሆን አለበት፡፡ ነገር ግን ሊሰጠን የታቀደው ቦታ መሠረት ልማት ጭራሽ ያልጎበኘው፣ ገደላ ገደልና ወንዛ ወንዝ ነው፤›› በማለት አርሶ አደሮቹ ይህንን ቦታ ለመረከብ ፍላጎት እንደሌላቸው አቶ መንገሻ አስታውቀዋል፡፡
አቶ መንገሻ፣ ‹‹ክፍለ ከተማው በቅድሚያ ሦስት ቦታዎች አሳይቶ ፍላጎታችንን መረዳት ነበረበት፡፡ ክፍለ ከተማው ግን በአንድ ጊዜ ይህንን ቦታ እንድንረከብ ዕጣ አወጣልን፡፡ ይህ በፍጹም ሕግን የተከተለ አይደለም፤›› በማለት አክለዋል፡፡
ኮሚቴው ቅሬታውን ለክፍለ ከተማው ቢያቀርብም፣ ክፍለ ከተማው ቅሬታውን ባለመቀበሉ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ ለማቅረብ እየተዘጋጀ መሆኑን አቶ መንገሻ አስረድተዋል፡፡
የቻይናው ግዙፍ ኩባንያ ኃጅዬን በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ጀሞ አካባቢ በ164 ሔክታር መሬት ላይ ዘመናዊ የሌዘር ኢንዱስትሪ ፓርክ በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡ በዚህ ፓርክ ውስጥ ከጫማ ፋብሪካዎች በተጨማሪ የቴክኒክና ሙያ ዩኒቨርሲቲ፣ የሠራተኞች መኖሪያ፣ የንግድ አገልግሎት መስጫ ተቋማት፣ አረንጓዴ ሥፍራዎች ግንባታ ያካተተ መሆኑን በሚያዚያ 2007 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ በተቀመጠበት ወቅት ተገልጿል፡፡
ይህ ኢንዱስትሪ ፓርክ ግንባታ ሲጠናቀቅ 30 ሺሕ ለሚደርሱ ሰዎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር፣ እስከ ሁለት ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ እንደሚያሰገኝም በወቅቱ ተገልጿል፡፡
ለዚህ ግንባታ መጓተት ኃጅዬን አርሶ አደሮች በወቅቱ ባለመነሳታቸው እንደሆነ ሲያስታውቅ የቆየ ሲሆን፣ አሁንም የተወሰኑ አርሶ አደሮች ካሳና ምትክ ቦታ እየጠበቁ መሆኑ ታውቋል፡፡
