ከኦሮሚያ ትልልቅ ከተሞች አንዱ የሆነው አዳማ (ናዝሬት) ከተማ በስድስት ክፍላተ ከተሞች እንዲደራጅ የክልሉ ካቢኔ ውሳኔ ማሳለፉ ታወቀ፡፡
የአዳማ ከተማ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ሰኞ የካቲት 13 ቀን 2009 ዓ.ም. ለከተማው ነዋሪዎች ባደረጉት ገለጻ በከተማው ከአገልግሎት ጋር በተያያዘ የሚስተዋለውን ኋላቀርነት ለማስወገድ ለሕዝቡ ቅሬታና ወቀሳ ተገቢ ምላሽ ለመስጠት፣ በአንድ አስተዳደር የሚመራውን አዳማ ከተማን በስድስት ክፍላተ ከተሞች ማደራጀት አስፈላጊ መሆኑ እንደታመነበት ገልጸዋል፡፡
ከ350 ሺሕ በላይ ሕዝብ እንደሚኖርበት የሚገለጸው አዳማ ከተማ፣ 14 የከተማና አራት የገጠር ቀበሌዎች እንዳሉትም ተጠቁሟል፡፡
ከተማው ያለበት ሁኔታ የመንግሥት ሥልጣን ያልተማከለበት በመሆኑ ወደ ሕዝቡ በመቅረብ ፈጣን ውሳኔና አገልግሎት መስጠት አለመቻሉን የገለጹት ከንቲባዋ፣ ሕዝቡ ተገቢ አገልግሎት እንዲያገኝና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን በአግባቡ ለመመለስ፣ በክፍለ ከተማ መደራጀቱ ተገቢ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የልማት ተሳታፊነትንና ተጠቃሚነትን ለማሳደግም እንደሚረዳም አክለዋል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ ከተማውን በክፍለ ከተማ ለማደራጀት መዋቅር አዘጋጅቶ መጨረሱን የጠቆሙት ከንቲባዋ፣ የሰው ኃይል ማደራጀቱ እየተጠናቀቀ በመሆኑ በቅርቡ ወደ ትግበራ እንደሚገባም አስረድተዋል፡፡ አዳማ የተቆረቆረችበትን 100ኛ ዓመት ባለፈው ወር በደማቅ ሁኔታ ማክበሯ ይታወሳል፡፡
