Quantcast
Channel: ተሟገት
Viewing all 1275 articles
Browse latest View live

የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ ልሳን ዋና አዘጋጅ ዋስትና ተከለከለ

$
0
0

‹ነገረ ኢትዮጵያ› በሚል ስያሜ ይታተም የነበረው የሰማያዊ ፓርቲ ልሳን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ አቶ ጌታቸው ሽፈራው የዋስትና ጥያቄው ውድቅ ተደረገ፡፡

ተከሶበት የነበረው የሽብር ተግባር ወንጀል ክስ ተቀይሮ ወደ መደበኛ ክስ በመቀየሩና የተጠቀሰበት የወንጀል ሕግ አንቀጽ 257 (ሀ እና መ) ዋስትና ባለመከልከሉ፣   አቶ ጌታቸው ያቀረበውን የዋስትና ጥያቄ መርምሮ ለታኅሳስ 25 ቀን 2009 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቶ የነበረው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት ነበር፡፡

ፍርድ ቤቱ በዕለቱ እንደገለጸው የአቶ ጌታቸውን ሕገ መንግሥታዊ የዋስትና መብት ጥያቄን ሲመረምር፣ ተከሳሹ ሕጋዊና መደበኛ የሚታወቅ የመኖሪያ አድራሻ እንዳለው ማረጋገጡን ከክርክሩ መረዳቱን ነው፡፡ ነገር ግን ዓቃቤ ሕግ ባቀረበው መቃወሚያ ተመሥርቶበት የነበረው የሽብር ድርጊት ወንጀል ተፈጽሟል የተባለው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሽብርተኛ ሆኖ ከተፈረጀው የግንቦት ሰባት ጋር በመሆኑ፣  በዋስትና ቢለቀቅ በተለያየ መንገድ ከአገር ሊወጣና ሊቀርብ እንደማይችል ማስረዳቱን ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡

በመሆኑም ለተከሳሹ የተቀየረው የሕግ አንቀጽ በመርህ ደረጃ ዋስትና የማይከለክል ቢሆንም፣ በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 67 (ሀ) መሠረት መመልከቱ አስፈላጊ መሆኑን እንዳመነበትም ገልጿል፡፡

በመሆኑም ዓቃቤ ሕግ እንዳቀረበው መቃወሚያና ተከሳሹ እንደሚያቀርብ የገለጻቸው መከላከያ ምስክሮች እንደክሱ ባያስረዱለት ሊያስቀጣው የሚችለውን ከፍተኛ የአሥር ዓመት እስራት ቅጣት በመፍራት፣ በተለያየ አኳኋን ወይም አቅጣጫ ከአገር ሊወጣ ይችላል የሚል ግንዛቤ ፍርድ ቤቱ መውሰዱን አስረድቷል፡፡ በመሆኑም በወ/መ/ሥ/ሥ/ቁጥር 67 (ሀ) መሠረት የዋስትና ጥያቄውን ውድቅ በማድረግ የመከላከያ ምስክሮቹን ለየካቲት 7 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲያቀርብ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

 

Standard (Image)

ኢሕአዴግ በግምገማ የማይጋለጡ የሙስና ወንጀሎችን በጥናት እፈትሻለሁ አለ

$
0
0

በገዥው ፓርቲ የግምገማ መድረኮች የማይጋለጡ ውስብስብ የሙስና ወንጀሎችን በልዩ ጥናት ፈትሾ እንደሚያወጣ፣ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ገለጸ፡፡

ኮሚቴው ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ ለሕዝብ በገባው ቃል መሠረት፣ ‹‹በጥልቀት የመታደስ›› ዘመቻው በጥሩ ሁኔታ በመተግበር ላይ መሆኑን ጠቁሟል፡፡

በዚህ ሒደት ፀረ ዴሞክራሲ፣ አድርባይነት፣ በትስስር የመሥራት አሠራሮችን በማረም በአባላቱና በአመራሮች መካከል ‹‹ጓዳዊ ትስስርን›› በማጣመር፣ መተማመንን በሚያጎለብት ሁኔታ መፈጸሙን ገልጿል፡፡

በድርጅቱ ውስጥ በተደረጉ ትግሎች ሙስናና ብልሹ አሠራሮች በየትኛውም ደረጃና መልኩ የሚገለጹ ቢሆንም፣ ያለምንም ምሕረት ፖለቲካዊ ትግል በማድረግ መጋለጣቸውን ያስረዳል፡፡ ከዚህ በመነሳትም ፖለቲካዊ፣ አስተዳደራዊና ሕጋዊ ዕርምጃዎች መወሰዳቸውን ይገልጻል፡፡

በግምገማ መድረክ የማይጋለጡ ከሙስና ውስብስብ ባህሪያት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በሚመለከት፣ በሁሉም ደረጃዎች ጥናቶችና ፍተሻዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ መወሰኑን አብራርቷል፡፡

በጋምቤላ የሰፋፊ እርሻዎች ኢንቨስትመንትን አስመልክቶ በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተዋቀረ ኮሚቴ ያጠናው ጥናት በቅርቡ ይፋ መሆኑን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

በዚህም ጥናት ከባንክ ብድር ጋር በተያያዙ ብልሹ አሠራሮችና ትስስር የቀረጥ ነፃ መብት መበዝበዝ እንደነበር ተገልጿል፡፡

ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ የፌዴራል ፖሊስ በሰጠው መግለጫ፣ በሙስና ወንጀል የተጠረጠሩ 130 ግለሰቦችና ባለሥልጣናት በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ይፋ አድርጓል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ የተያዙት ከመንግሥት ዕቃ ግዥ፣ ከቤቶች ልማት፣ ከመሬት ልማት፣ ከባንክ ሥራዎችና ከአክሲዮን ኩባንያዎች፣ ከታክስ ማጭበርበር ጋር መሆኑን ገልጿል፡፡   

 

Standard (Image)

መሬት የማስተዳደር ኃላፊነቱን ያጣው ኤጀንሲ ትኩረቱን ባለሀብቶችን መደገፍ ላይ አደረገ

$
0
0

- ለባለሀብቶች የተላለፈ መሬት ሙሉ በሙሉ ባለመልማቱ 11.3 ቢሊዮን ብር ታጣ

ከክልሎች በውክልና የወሰደውን የእርሻ ኢንቨስትመንት መሬት መልሶ ለክልሎች እንዲያስረክብ የታዘዘው የኢትዮጵያ የግብርና ኢንቨስትመንት መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ፣ ትኩረቱን ለባለሀብቶች ኤክስቴንሽን አገልግሎት መስጠት ላይ አድርጓል፡፡

በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 283/2005 የተቋቋመው የኢትዮጵያ የግብርና ኢንቨስትመንት መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ፣ በውክልና የወሰደውን መሬት ለክልሎች እንዲመልስ ታዟል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በቅርቡ በመሩት ውይይትና የእርሻ ኢንቨስትመንት ላይ በተካሄደው ጥናት፣ መሬት የማስተዳደር ኃላፊነት ለክልሎች እንዲመልስ መወሰኑ ይታወሳል፡፡

‹‹ቀደም ሲል መሬት በውክልና በመግባቢያ ሰነድ ከከልሎች ተወስዶ በፌዴራል ደረጃ ለባለሀብቶች የሚሰጥበትና የሚተዳደርበት ሥርዓት በሕገ መንግሥቱ ከተደነገጉ መሠረታዊ ጉዳዮችና አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ጋር ተያይዞ በኅብረተሰቡ ዘንድ ብዥታ እየፈጠረ በመሆኑ፣ መሬት የማስተዳደርና ለባለሀብት የማስተላለፍ ተግባር በክልሎች ባለቤትነት ይፈጸም፤›› ሲል በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስተባባሪነት የተካሄደው ጥናት ያመለክታል፡፡

የፌዴራል መንግሥት በዚህ ረገድ የክልሎችን አቅም ለመገንባት፣ ከክልሎች ጋር ተቀናጅቶና ተባብሮ ኢንቨስትመንቱ የተሳለጠ የማድረግ ሥራ እንዲሠራ ውሳኔ ተላልፏል፡፡ በዚህ ውሳኔ መሠረት በእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ሚኒስቴር ሥር የሚገኘው የኢትዮጵያ ግብርና ኢንቨስትመንትና መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ ትልቁን ሥራውን አጥቷል፡፡ የፌዴራል መንግሥት እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው መሬቱ በቀጥታ በክልሎች ቢተዳደር የተሻለ የአሠራር መሻሻል ይኖራል የሚል አስተያየት ከተለያዩ አቅጣጫዎች በመሰንዘሩ ነው፡፡

በዚህ መሠረት ኤጀንሲው ታኅሳስ 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ይፋ ባደረገው የሰፋፊ ግብርና ኢንቨስትመንት ኤክስቴንሽን አገልግሎት አተገባበር ማኑዋል ረቂቅ ሰነድ፣ የግብርና ኢንቨስትመንትን እንደሚደግፍ ገልጿል፡፡

የዚህ የኤክስቴንሽን አገልግሎት ተግባራዊ ለማድረግ ያስፈለበትን ምክንያት የባለሀብቱን ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ለማሻሻል፣ የባለሙያና የሠራተኞች ክህሎት ለማሳደግ፣ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ለማሻሻል፣ የኤክስፖርት ምርቶችን ማሳደግ የሚሉት ይገኙበታል፡፡

በፌዴራልና በክልሎች 2.5 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ለባለሀብቶች ቢተላለፍም፣ ዘርፉ በበርካታ አስተዳደራዊ ችግሮች በመተብተቡ ምርታማነት ሊያድግ አልቻለም፡፡ ኤጀንሲው ባዘጋጀው ረቂቅ ሰነድ ላይ ከተላለፈው መሬት ውስጥ በአጠቃላይ ወደ ልማት የገባው 983,537.06 ሔክታር መሬት ሲሆን፣ የተገኘው ምርት 1,647,021 ቶን ነው፡፡ የተላለፈው መሬት በሙሉ ቢለማ የሚጠበቀው ምርት 2,770,000 ቶን ይሆን እንደነበር ረቂቅ ሰነዱ ያመለክታል፡፡ ነገር ግን ሊመረት ይገባ የነበው 1.2 ሚሊዮን ቶን ምርት ሳይመረት ቀርቷል፡፡ ይህ ምርት በገንዘብ ሲተመን 11.3 ቢሊዮን ብር መሆኑንና ይህ ገንዘብ መታጣቱንም ሰነዱ አመልክቷል፡፡

በዚህ መሠረት ኤጀንሲው መሬት ከማስተዳደር ይልቅ ትኩረቱን ባለሀብቶችን መደገፍ ላይ አድርጓል፡፡ የኤክስቴንሽን አገልግሎቱን ተግባራዊ ለማድረግ በፌዴራልና በክልሎች ዓብይ ኮሚቴዎች እንደሚቋቋሙና ረቂቅ ሰነዱም በአሁኑ ወቅት በውይይት ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡

በዚህ ጉዳይ ላይ የኢትዮጵያ የግብርና ኢንቨስትመንት መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ አበራ ሙላት አስተያየት እንዲሰጡ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡ 

Standard (Image)

የሰመራ ኤርፖርት ማሻሻያ ፕሮጀክት በ268 ሚሊዮን ብር ወጪ እየተካሄደ ነው

$
0
0

የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት የአፋር ክልል ዋና ከተማ በሆነችው ሰመራ የሚገኘውን ኤርፖርት የማሻሻያ ግንባታ በ268 ሚሊዮን ብር ወጪ በማካሄድ ላይ ነው፡፡

ከ1990ዎቹ ጀምሮ የሰመራ አውሮፕላን ማረፊያ ሜዳ መደበኛ ያልሆኑ የአነስተኛ አውሮፕላን በረራዎች ሲያስተናግድ ቆይቷል፡፡ የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት የማሻሻያ ሥራ በማከናወን፣ ሁለት ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የጠጠር የአውሮፕላን ማረፊያና አነስተኛ ጊዜያዊ ተርሚናል ገንብቶ በታኅሳስ 2006 ዓ.ም. መደበኛ በረራ አገልግሎት ማስተናገድ ጀምሯል፡፡ በወቅቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቦምባርዲየር Q400 አውሮፕላን በሳምንት ሦስት ቀን መደበኛ በረራ መስጠት ጀምሮ፣ የአካባቢው ሕዝብ የአየር ትራንስፖርት ፍላጎት በማደጉ አየር መንገዱ በየዕለቱ የበረራ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት የኮሙዩኒኬሽንና ሕዝብ ግንኙነት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወንድም ተክሉ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ የአፋር ክልል የኢኮኖሚ ዕድገትና ያሉትን የቱሪስት መስህቦች በመመልከት እንዲሁም የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር መቀመጫ ከመሆኗ ጋር ተያይዞ፣ የሰመራ ኤርፖርትን ማሻሻል አስፈላጊ እንደሆነ ታምኖበታል፡፡ በአፋር ክልል ኢንቨስትመንትና የቱሪስት ፍሰት እያደገ እንደመጣ አቶ ወንድም ያስረዳሉ፡፡

በክልሉ በጨው ምርት፣ በፖታሽ ማዕድንና በወርቅ ፍለጋ በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎች ተሰማርተው ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ ላይ ይገኛሉ፡፡ የፌዴራል መንግሥትም ይህን በመመልከት በክልሉ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ ከፍተኛ ሙቀት ባለበት በዚህ ክልል የመከላከያ ኮንስትራክሽን ድርጅት ከኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን በገባው ውል መሠረት፣ የአስፋልትና የሲሚንቶ ኮንክሪት መንገዶች በመገንባት ላይ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅትም ክልሉን በአየር ትራንስፖርት ለማገናኘት የሰመራ ኤርፖርትን ደረጃ ለማሳደግ በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛል፡፡ የኤርፖርት ማሻሻያ ሥራ የመጀመሪያ ክፍል የሆነው የአውሮፕላን ማረፊያ ሜዳውን ከጠጠር ወደ ኮንክሪት አስፋልት ማሳደግ ነው፡፡ በመሆኑም ድርጅቱ ያወጣውን ጨረታ አገር በቀል ኩባንያ የሆነው አፍሮ ጽዮን ኮንስትራክሽን አሸንፎ፣ የአውሮፕላን ማኮብኮቢያና ማረፊያ ሜዳውን በአስፋልት ኮንክሪት በ268 ሚሊዮን ብር ለመሥራት ውል ፈርሞ ግንባታውን በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡

የአውሮፕላን ማረፊያው 2.5 ኪሎ ሜትር ርዝመትና 60 ሜትር ስፋት እንዳለው የገለጹት አቶ ወንድም፣ ቦይንግ 737 የመሳሰሉ ጄት አውሮፕላኖችን ማሳረፍ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለሚሰጠው ዕለታዊ መደበኛ አገልግሎት ምቹ እንደሚሆን፣ መደበኛ ያልሆኑ በረራዎች አገልግሎት የሚሰጡ የግል አየር መንገዶችም በኤርፖርቱ መጠቀም እንደሚችሉ አመልክተዋል፡፡

በአፍሮ ጽዮን ኮንስትራክሽን የሰመራ ኤርፖርት ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ አቶ ግዛቸው ጌጤ፣ የአውሮፕላን ሜዳ ግንባታ ሥራው መስከረም 2008 ዓ.ም. መጀመሩንና በአሁኑ ወቅት የግንባታው 70 በመቶ መጠናቀቁን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በኮንትራት ውሉ ግንባታው በነሐሴ 2009 ዓ.ም. ሙሉ በሙሉ መጠናቀቅ ያለበት ቢሆንም፣ ሰመራ 12ኛውን የብሔር ብሔረሰቦች በዓል ኅዳር 2010 ዓ.ም. የምታስተናግድ በመሆኗ አፍሮ ጽዮን ኮንስትራክሽን የአውሮፕላን ማረፊያ ሜዳውን ግንባታ ቀደም ብሎ በሰኔ 2009 ዓ.ም. ለማጠናቀቅ ርብርብ በማድረግ ላይ መሆኑን አቶ ግዛቸው ተናግረዋል፡፡ ሳባ ኢንጅነሪንግ የተባለው አገር በቀል ኩባንያ የፕሮጀክቱ አማካሪ ነው፡፡

የሰመራ ኤርፖርት ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳንኤል አምባቸው፣ የሰመራ ኤርፖርት የአውሮፕላን ማረፊያ ሜዳ በመገንባት ላይ ያለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰጠው መደበኛ የበረራ አገልግሎት ሳይስተጓጎል እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ የክልሉ መንግሥት የኤርፖርት ግንባታውን እንደ ራሱ ፕሮጀክት በመመልከት አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ ላይ መሆኑንም አቶ ዳንኤል ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ለሰመራ ኤርፖርት ዘመናዊ የመንገደኞች ተርሚናል ግንባታ ለማካሄድ የዲዛይን ሥራ ተጠናቆ ግንባታውን የሚያካሂድ ኮንትራክተር ለመቅጠር ጨረታ መውጣቱን ከአቶ ወንድም ማብራሪያ ለመረዳት ተችሏል፡፡ በአንድ ጊዜ 170 መንገደኞች ማስተናገድ የሚችል ዘመናዊ ተርሚናል ግንባታ በ2009 ዓ.ም. እንደሚጀመር የገለጹት አቶ ወንድም፣ ተርሚናሉ የአካባቢውን ኅብረተሰብ አኗኗርና ባህል የሚያንፀባርቅ እንደሚሆን አክለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሲቪል አቭዬሽን ባለሥልጣን በበኩሉ የአየር ትራፊክ መቆጣጠሪያ በመገንባት ላይ ነው፡፡ ናሽናል ኦይል ካምፓኒ (ኖክ) የአውሮፕላን ነዳጅ ማቅረቢያ ጣቢያ ለመገንባት በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡

የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት 22 ኤርፖርቶችን ያስተዳድራል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 20 የሚሆኑት የአስፋልት መንደርደሪያ ያላቸው ሲሆኑ፣ አራቱ (አዲስ አበባ፣ ድሬዳዋ፣ መቀሌና ባህር ዳር) ዓለም አቀፍ ኤርፖርት ናቸው፡፡ ሁለቱ በጠጠር ሜዳ በረራዎችን ያስተናግዳሉ፡፡

በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ የኤርፖርቶችን ቁጥር ወደ 30 ለማሳደግ፣ ከዚህ ውስጥ 25ቱን የአስፋልት ሜዳ ያላቸው እንዲሆኑ ድርጅቱ ሰፊ ሥራ በማከናወን ላይ መሆኑን አቶ ወንድም ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የሰመራ፣ የሐዋሳ፣ የጂንካ፣ የሮቤ፣ የሽሬ፣ የደምቢዶሎና የነቀምቴ ኤርፖርቶች ግንባታ በመካሄድ ላይ ነው፡፡ በላሊበላ፣ በባህር ዳርና በጎንደር ኤርፖርቶች የተለያዩ የማሻሻያ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው፡፡ የአገር ውስጥ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ፍላጎት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን የገለጹት አቶ ወንድም፣ የአገር ውስጥ መንገደኞች ፍሰት በየዓመቱ 20 በመቶ በማደግ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ2008 ዓ.ም. ከሦስት ሚሊዮን በላይ መንገደኞችን በአገር ውስጥ በረራዎች አጓጉዟል፡፡ አየር መንገዱ 20 የአገር ውስጥ በረራ መዳረሻዎች አሉት፡፡ ‹‹ይህ የሕዝቡ የመክፈል አቅም መጨመሩን ያሳያል፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው አገሪቱ ተከታታይና ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ለማስገንዘብ በመቻሏ ነው፤›› ያሉት አቶ ወንድም፣ የክልል ኤርፖርቶች ከገቢ አንፃር ለድርጅቱ ትርፋማ ባይሆኑም መንግሥት ካስቀመጠው የአየር ትራንስፖርትን በሁሉም ክልሎች ተደራሽ የማድረግ አቅጣጫ በመነሳት፣ ድርጅቱ በክልሎች ኤርፖርቶችን መገንባትና የማሻሻል ሥራ እንደሚሠራ አስረድተዋል፡፡

‹‹በቀጥታ በገንዘብ ተጠቃሚ ባንሆንም የአየር ትራንስፖርት የክልሎችን የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ዘርፎችን የሚያነቃቃ በመሆኑ የክልል ኤርፖርቶች ላይ ኢንቨስት እናደርጋለን፡፡ የሐዋሳ ኤርፖርት ግንባታ ሲጀመር ለአዲስ አበባ ካለው ቅርበት አንፃር አስፈላጊነቱ ላይ ጥያቄ ያነሱ ወገኖች ነበሩ፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሳምንት የሦስት ቀናት በረራ አገልግሎት መስጠት ጀምሮ ዛሬ በየዕለቱ እየበረረ አውሮፕላኑ ሙሉ ነው፡፡ ኤርፖርቱ ከጅምሩ ለክልሉ ኢንቨስትመንትና ቱሪዝም ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል፤›› ያሉት አቶ ወንድም፣ በክልል የሚገነቡ ኤርፖርቶች በገንዘብ የሚያስገቡት ገቢ ሳይሆን መታየት ያለበት ለክልሎች ንግድ፣ ኢንቨስትመንትና ቱሪዝም ዕድገት በሚያደርጉት አስተዋጽኦ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

በሰመራ ከተማ ከኤርፖርቱ በተጨማሪ ዘመናዊ ሁለገብ ስታዲየም፣ የእንግዳ ማረፊያዎችና መንገዶች በመገንባት ላይ መሆናቸውን ለመረዳት ተችሏል፡፡                

Standard (Image)

ሃይማኖታዊ መንግሥት ለማቋቋም ተንቀሳቅሰዋል የተባሉ 20 ተከሳሾች የቅጣት ውሳኔ ተላለፈባቸው

$
0
0

ከሁለት ዓመት በፊት ‹‹ሃይማኖታዊ መንግሥት ማቋቋም›› የሚል ፖለቲካዊ ግብ በማስቀመጥ ሲንቀሳቀሱ ተገኝተዋል ተብለው ክስ ተመሥርቶባቸው ሲከራከሩ የከረሙት የቢላል ሬዲዮ ዋና አዘጋጅን ጨምሮ 20 ተከሳሾች፣ ማክሰኞ ታኅሳስ 25 ቀን 2009 ዓ.ም. የቅጣት ውሳኔ ተላለፈባቸው፡፡

በወቅቱ በሽብር ተግባር ወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት በመታየት ላይ የነበሩትን እነ አቡበከር አህመድንና እነ ኤልያስ ከድር የተባሉ ተከሳሾችን ከእስር ለማስፈታት ሲንቀሳቀሱ፣ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው በክሱ ላይ የተጠቀሱት የቢላል ሬዲዮ ዋና አዘጋጅ ካሊድ መሐመድና ጋዜጠኛ ዳርሰማ ሶሪን ጨምሮ 20 ግለሰቦች ናቸው፡፡

በወቅቱ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የነበሩትና ‘የሙስሊሙ ማኅበረሰብ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ’ እየተባሉ የሚጠሩትን እነ አቡበከር አህመድን መንግሥት ማሰሩ ትክክል እንዳልሆነ እየገለጹ፣ ፍርደኞቹ ቅስቀሳ ያደርጉ እንደነበር የቅጣት ውሳኔው ያስረዳል፡፡

ሕዝበ ሙስሊሙን ወደ አመፅ በማስገባት የሽብር ተግባር በመፈጸምና በመንግሥት ላይ ጫና በመፍጠር፣ መንግሥት አማራጭ ሲያጣ እንዲፈታቸው ለማድረግ በራሪ ወረቀቶችን አዘጋጅተው እንደነበር ክሱ ይጠቁማል፡፡ በአዲስ አበባ፣ በጅማና በወልቂጤ ከተሞች በራሪ ወረቀቶችን በመበተን፣ ሕገወጥ ሠልፎችን በማዘጋጀት የአመፅ ቅስቀሳ ለማድረግ ሃያዎቹም ፍርደኞች ተሳትፎ ማድረጋቸውን
ፍርድ ቤቱ በቅጣት ውሳኔው ዘርዝሮ አቅርቦ ነበር፡፡

የቢላል ሬዲዮ ዋና አዘጋጅ ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ በአዲስ አበባ አንዋር፣ ቤኒንና አወልያ መስጊዶች በተካሄዱ አመፆች ላይ በመገኘት ኅብረተሰቡን ለአመፅ የሚያነሳሱ ቅስቀሳዎችን ማለትም ‹‹ድምፃችን ይሰማ፣ የታሰሩ ኮሚቴዎች ይፈቱ፣ የአህባሽ አስተምህሮን መንግሥት በኃይል ሊጭንብን አይገባም…›› በማለት ሲሳተፉ እንደነበር ክሱ ያብራራል፡፡ ሌሎቹም ፍርደኞች ተመሳሳይ ድርጊቶችን በተናጠልና በቡድን በመሆን መፈጸማቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ማስፈሩን፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ታኅሳስ 25 ቀን 2009 ዓ.ም. የሰጠው የቅጣት ውሳኔ ያስረዳል፡፡

ዓቃቤ ሕግ እንደ ክሱ የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን በማቅረብ ማስረዳቱን ፍርድ ቤቱ ገልጾ፣ ፍርደኞቹ እንዲከላከሉ ውሳኔ ሰጥቶ ነበር፡፡ ፍርደኞቹም የተከላከሉ ቢሆንም፣ የዓቃቤ ሕግን ክስና የምስክሮች ቃል ማስተባበል እንዳልቻሉ ተነግሯቸው የጥፋተኝነት ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡ በመሆኑም ከፍርደኛ ዳርሰማ ሶሪ ባንቃሺ በስተቀር ሁሉም ፍርደኞች ካቀረቡት የቅጣት ማቅለያ ሐሳብ፣ ከእያንዳንዳቸው ሁለት ማቅለያ ተወስዶላቸዋል፡፡

ዳርሰማ ሶሪ ግን ሦስት ማቅለያ ተወስዶለታል፡፡ በመሆኑም ፍርደኞቹ እያንዳንዳቸው በአምስት ዓመት ከስድስት ወራት ጽኑ እስራት እንዲቀጡ፣ ዳርሰማ ሶሪ ግን በአራት ዓመታት ከአምስት ወራት ጽኑ እስራት እንዲቀጣ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ 

 

Standard (Image)

የአዲስ አበባ ምክር ቤት ማስተር ፕላኑን ሊያፀድቅ ነው

$
0
0

በብዙ ውጣ ውረድ ውስጥ ያለፈው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አሥረኛው ማስተር ፕላን፣ በሚቀጥሉት ጥቂት ሳምንታት ውስጥ ለምክር ቤት ቀርቦ እንደሚፀድቅ ታወቀ፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ ማስተር ፕላኑ ከመፅደቁ በፊት የወረዳ፣ የክፍላተ ከተማና ማዕከል የሚገኘው ዋናው ምክር ቤት ጋር በጋራ እንዲወያዩበት ማድረጉን ገልጿል፡፡

ታኅሳስ 22 ቀን 2009 ዓ.ም በተካሄደው ውይይት በሚቀጥሉት አሥር ዓመታት ወይም 25 ዓመታት ተግባራዊ የሚደረገው ማስተር ፕላን ይዘትና ይዟቸው የሚመጣቸው ተስፋዎች ላይ፣ የቀድሞው የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ፕሮጀክት ኃላፊ አቶ ማቴዎስ አስፋው ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

አዲስ አበባ ከተማ በ130 ዓመት ታሪኳ ዘጠኝ ማስተር ፕላን አስተናግዳለች፡፡ በአሁኑ ወቅት የተጠናቀቀው አሥረኛው ማስተር ፕላን ከሌሎች ዘጠኝ ማስተር ፕላኖች ጋር ሲነፃፀር በስፋትም በጥልቀትም የተለየ ነው ተብሏል፡፡

ዘጠነኛውና አሥረኛው ማስተር ፕላን በአገር ውስጥ ባለሙያዎች፣ የተቀሩት ስምንት ማስተር ፕላኖች ደግሞ በውጭ አገር ባለሙያዎች የተዘጋጁ ናቸው፡፡

አቶ ማቴዎስ በዘጠነኛውና በአሥረኛው ማስተር ፕላን ዋነኛ ተዋናይና መሪ ሆነው የሠሩ ሲሆን፣ የአሥረኛው ማስተር ዝግጅት በመጠናቀቁ በቅርቡ የአዲስ አበባ ከተማ ፕላን ኮሚሽነር ሆነው ተሹመዋል፡፡

አዲሱ ፕላን ኮሚሽን ማስተር ፕላኑ በአግባብ መተግበሩን የመቆጣጠር ሥልጣንና ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡

አቶ ማቴዎስ ቅዳሜ ታኅሳስ 22 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሄደው ውይይት ቀጣዩ የአዲስ አበባ ከተማ የሕዝብ ዕድገትና የኢኮኖሚ እምርታ ሊያስተናግድ በሚችል ደረጃ፣ የአፍሪካ ዲፕሎማቲክ መቀመጫ መሆኗን በሚገባ በምታረጋግጥበት መንገድ መዘጋጀቱን አመልክተዋል፡፡

ከዚህ ቀደም ወደ ጎን ስትለጠጥ ቆይታ ያላትንም 54 ሺሕ ሔክታር መሬት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ግንባታ ያካሄደችበት አዲስ አበባ፣ ‹‹በአዲሱ ማስተር ፕላን ወደ ጎን መለጠጧን አቁማ ወደ ላይ ከፍ ማለት ትጀምራለች፤›› ሲሉ አቶ ማቴዎስ ገልጸዋል፡፡

በሚቀጥሉት አሥር ዓመታት የአዲስ አበባ ሕዝብ ቁጥር አሁን ካለበት አራት ሚሊዮን በተጨማሪ፣ 1.3 ሚሊዮን ሕዝብ አዲስ ነዋሪ ሆኖ እንደሚመዘገብና ይህ ሁሉ ሕዝብ በመሀል ከተማ እንደሚሰፍር አቶ ማቴዎስ ተናግረዋል፡፡

ለዚህም ዕቅድ መሳካት መሃል ከተማው (ዞን አንድ) ውስጥ በርካታ ቤቶች የሚገነቡ ከመሆኑ በላይ፣ አራት ደረጃ በወጣላቸው ዞኖች ውስጥ ማንኛውም ባለሀብት የሚገነባው ሕንፃ መኖሪያ ቤቶችን ማካተት ይጠበቅበታል፡፡

አቶ ማቴዎስ እንዳሉት ከመንግሥት ተቋማት፣ ከደኅንነትና ወታደራዊ ተቋማት፣ ከሆስፒታሎች፣ ከእምነት ተቋማት፣ ከሆቴሎችና ከትምህርት ቤቶች ግንባታ በስተቀር በሚካሄዱ ማናቸውም ሕንፃዎች መኖሪያ ቤቶችን ማካተታቸው የግድ ነው፡፡

በዞን አንድ 30 በመቶ፣ በዞን ሁለት 40 በመቶ፣ በዞን ሦስት 50 በመቶ፣ በዞን አራት 60 በመቶ  የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ መካተት አለበት ተብሏል፡፡

‹‹በመሀል ከተማ ስምንት ሚሊዮን ሕዝብ የማስፈር ዕቅድ ተይዟል፡፡ ይህን ልናደርግ የምንችለው ነባርና ያረጁ ግንባታዎችን አፍርሰን ነው፤›› ሲሉ አቶ ማቴዎስ ጠቁመዋል፡፡

‹‹ዞን አንድ ላይ ማለትም (ፒያሳ፣ ብሔራዊ፣ ሜክሲኮና ለገሃር አካባቢዎች) የሚገነቡ ሕንፃዎች በአንድ ሔክታር 150 ቤቶች መያዝ ይኖርባቸዋል፤›› ሲሉም አቶ ማቴዎስ ቀጣዩን አቅጣጫ ጠቁመዋል፡፡

በዚህ ሒደት ግን የአንድ መኖሪያ ቤት ካሬ ሜትር ስፋት ላይ ማሻሻያ ተደርጓል፡፡ በተካሄደው ማሻሻያ አንድ መኖሪያ ቤት ዝቅተኛው የሚያርፍበት ቦታ 30 ካሬ ሜትር የነበረው፣ በአዲሱ ማስተር ፕላን 90 ካሬ ሜትር እንዲሆን ተደርጓል፡፡

‹‹በከፍተኛ ጥግግት አዲስ አበባን አየር ላይ ገንብተን ሕዝብ የተሸለ ኑሮ እንዲኖር እናደርጋለን፤›› ሲሉ አቶ ማቴዎስ አስረድተዋል፡፡

አሁን ያለው የአዲስ አበባ ከተማ ገጽታ መሠረታዊ በሚባል ደረጃ ይቀይራል የተባለው ማስተር ፕላን በመሬት አጠቃቀም፣ በመኖሪያ ቤቶች ግንባታ፣ በትራንስፖርት መሠረተ ልማት ግንባታ፣ በአረንጓዴ ቦታዎች ልማት፣ በቅርስ አጠባበቅ፣ ወዘተ መሠረታዊ ለውጥ ያመጣል ያለውን ዕቅድ ይዞ ቀርቧል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በአሥር ዓመት ጊዜ ውስጥ በርካታ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎች፣ ዓለም አቀፍ ደረጃ የጠበቁ የጤና ተቋማትና የአፍሪካ ባህል ማዕከልን ለመገንባት ታቅዷል፡፡

በማሻሻያ ደረጃም ለከተማው ነዋሪዎች አስቸጋሪ ሁኔታ በፈጠሩት በቀላል ባቡር መስመሮችና በቀለበት መንገድ ላይ ተጨማሪ የእግረኛ መሻገሪያ ድልድዮች ለመገንባት ታስቧል፡፡

በ1994 ዓ.ም ተግባራዊ መደረግ የጀመረው ዘጠነኛው ማስተር ፕላን በ2006 ዓ.ም የመጠቀሚያ ጊዜው አብቅቷል፡፡ አሥረኛው ማስተር ፕላን ከኦሮሚያ ልዩ ዞን ጋር አቀናጅቶ ለማካሄድ በርካታ ሥራዎች የተሠሩ ቢሆንም፣ ከኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ በመቅረቡ እንዲቀር ተደርጓል፡፡

በዚህ ምክንያት ባለፉት አራት ዓመታት አዲስ አበባ ይፋ ማስተር ፕላን ሳይኖራት ቆይቷል፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን ሥራዎቹ በመጠናቀቃቸው ለምክር ቤቱ ፀድቆ ተግባራዊ ይሆናል ተብሏል፡፡

 

Standard (Image)

በእነ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ አስተባባሪነት ቂሊንጦን በማቃጠልና ታራሚዎችን በመግደል የተጠረጠሩ 121 እስረኞች ተከሰሱ

$
0
0

ከጥር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ከእስር ለማምለጥ ከዶ/ር ፍቅሩ ማሩና ከተለያዩ እስረኞች ጋር ሲወያዩ የከረሙ ታራሚዎ፣ ነሐሴ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ቂሊንጦ ጊዜያዊ የተከሳሾች ማረፊያ ቤትን በማቃጠልና የ23 እስረኞችን ሕይወት አጥፍተዋል የተባሉ 121 እስረኞች ተከሰሱ፡፡

የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ለፍርድ ቤት ያቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው፣ በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ በሚገኘው ቂሊንጦ ጊዜያዊ ማረፊያ ቤት ውስጥ የሚገኙ እስረኞች ለስምንት ወራት ሴራ ሲጠነስሱ ከርመዋል፡፡ ዶ/ር ፍቅሩ፣ ኢብራሒም ካሚልና ሸምሱ ሰዒድ የተባሉት እስረኞች ሌሎቹ እስረኞች ‹‹የዱርዬው ቡድን›› በመባል በማረሚያ ቤቱ ውስጥ በተቋቋመው ቡድን ውስጥ እንዲታቀፉ ሲያወያዩ ነበር፡፡ ለማረሚያ ቤቱ ፖሊስ መረጃ ያቀብላሉ ብለው የጠረጠሯቸውን እስረኞች በማረሚያ ቤቱ በሚገኝ ፌሮ ብረትና ማንኛውም ቁሳቁስ ነገር ደብድበው በማቁሰልና በመግደል እንዲቃጠሉ ማድረጋቸውንም ክሱ ያብራራል፡፡

ተከሳሾቹ በተለያዩ የወንጀል ድርጊት ተከሰው ክሳቸውን በመከታተል ላይ ያሉ ሲሆኑ፣ በ2008 ዓ.ም. መጨረሻዎቹ ወራት ላይ ተከስቶ የነበረውን አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) ተላላፊ በሽታ ምክንያት፣ ማረሚያ ቤቱ ለአንድ ቀን ከታራሚ ቤተሰቦች ምግብ እንዳይገባ በመከልከሉ ሳቢያ ቡድኑ እስረኞቹን በማስተባበር የማረሚያ ቤቱን ምግብ እንዳይበሉ አድማ ማስመታቱን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ገልጿል፡፡

ከጥር ወር ጀምሮ ለስምንት ወራት ‹‹ከእስር እናመልጣለን›› የሚል ዕቅድ ነድፈው ሲያሴሩ መቆየታቸውን የሚገልጸው የዓቃቤ ሕግ ክስ፣ ማረሚያ ቤቱ ነሐሴ 27  ቀን 2008 ዓ.ም. ከውጭ ምግብ እንዳይገባ መከልከሉን ምክንያት በማድረግ ቃጠሎውን መፈጸማቸውን፣ እስረኞችን በአሰቃቂ ሁኔታ በፌሮ ብረትና በተለያዩ ቁሳቁሶች ደብድበው በመግደል እንዲቃጠሉ ማድረጋቸውን በክሱ ዘርዝሯል፡፡

ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ክስ የመሠረተባቸው 121 እስረኞች በጋራና በተናጠል በመሆን የዱርዬው ቡድን የሚሠራውንና የሚያደርገውን ሚስጥራዊ እንቅስቃሴ ለማረሚያ ቤቱ ፖሊሶችና ኃላፊዎች ይናገራሉ በማለት የጠረጠሯቸውን 23 እስረኞችን (ስማቸው ተጠቅሷል) ቀጥቅጠው በመግደል፣ በማረሚያ ቤቱ ቀድመው በእሳት የተቀጣጠሉ የዞን ሰባት ሁለት መኝታ ቤቶች ውስጥ በመጣል እንዳቃጠሏቸው ክሱ ያብራራል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ሦስት ክሶችን በቅጽል ስሙ ዊዚ በሚባለው ያሬድ ሁሴን ላይ የመሠረተ ሲሆን፣ ሌሎች ስምንት ክሶችን በጋራ አድርጎ መሥርቷል፡፡ ሁሉም ተከሳሾች (121) የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1ሀናለ) እና 539 (1ሀናሐ) ሥር የተደነገገውን በመተላለፍ፣ ከባድ የሰው መግደል ወንጀል መፈጸማቸውንና ለዚህም ድርጊት በዋናነት የሚወያዩት ከዶ/ር ፍቅሩ ማሩ፣ ከማስረሻ ሰጤና ከሌሎችም እስረኞች ጋር በመመካከር መሆኑን ክሱ ያብራራል፡፡

ከተከሳሾቹ መካከል ቴዎድሮስ ዳንኤል፣ ብስራት አበራ፣ አራጋው ሞገስ፣ የአብስራ ብርሃኑ፣ ዳዊት በላይነህ፣ ገብረ ሚካኤል ገብረ ሥላሴ የተባሉ ተከሳሾች ከጥር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በማረሚያ ቤቱ ከዶ/ር ፍቅሩ፣ ከማስረሻ ሰጤና ከሚስባህ ከድር ጋር ዕቅድ በመያዝና ለማስፈጸም የተለያዩ ዝግጅቶችን በማድረግ ‹‹የዱርዬው ቡድን››ን ማቋቋማቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡

ተከሳሾቹ (121) በቡድኑ ሥር አባል እንዲሆኑ በማድረግና ሌሎችንም እንዲያደራጁ፣ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ አመፅ በመፍጠር ምቹ ሁኔታዎችን እንዲያመቻቹ 500,000 ብር እንደተሰጣቸው ክሱ ይገልጻል፡፡ ገንዘቡ የተሰጣቸው ለፖሊስ መረጃዎችን የሚያቀብሉ እስረኞችን እንዲገድሉ መሆኑንም ክሱ ያስረዳል፡፡ ተከሳሾቹ እስረኞችን በማደራጀት በመዘጋጀት ላይ እያሉ አተትን ምክንያት በማድረግ የተከሳሾች ቤተሰቦች ምግብ እንዳያስገቡ ማረሚያ ቤቱ ሲያሳውቅ፣ ዱርዬው ቡድን እስረኞችን በመሰብሰብ የማረሚያ ቤቱን ውሳኔ እንዲቃወሙና ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. አመፅ በማስነሳት ድርጊቱ እንዲፈጸም ማድረጋቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ አስፍሯል፡፡

ተከሳሾቹ በተናጠል፣ በጋራና በቡድን በመሆን በማረሚያ ቤቱ ላይ በፈጸሙት የእሳት ቃጠሎና የሰው መግደል ወንጀል የ23 ሰዎች ሕይወት ማለፉንና 15 ሚሊዮን ብር ግምት ያለው ንብረት ሊወድም መቻሉን ክሱ ያብራራል፡፡ በመሆኑም 121 ተከሳሾች በፈጸሙት ከባድ የሰው መግደልና በንብረት ላይ ጉዳት ማድረስ ወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸዋል፡፡

የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በፌዴራል ማረሚያ ቤት ቂሊንጦ ጊዜያዊ እስረኞች ማረፊያ ቤትን ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. በማቃጠል በተጠረጠሩ፣ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ 38 ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ መመሥረቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ዶ/ር ፍቅሩ የአዲስ ካርዲዮቫስኩላር ማዕከል መሥራችና ባለድርሻ ናቸው፡፡ በእነ አቶ መላኩ ፈንታ የሙስና መዝገብ ተከሰው በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ 

Standard (Image)

የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት 40 በመቶ ድርሻ ለመሸጥ ድርድር መጀመሩ ተሰማ

$
0
0

- የመርከብ አገልግሎት ዋነኛውን ድርሻ ይይዛል

ከመንግሥት የልማት ድርጅቶች ውስጥ በግዙፍነታቸው ከሚጠቀሱ ተቋማት መካከል አንዱ የሆነው የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ኢንተርፕራይዝ፣ 40 በመቶ የሚሆነውን ድርሻ ለመሸጥ ድርድር እየተካሄደ ነው፡፡

አራት የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን በመዋሀድ እንደ አዲስ የተቋቋመውን ኢንተርፕራይዝ 40 በመቶ የሚሆነውን የባለቤትነት ድርሻ በመሸጥ ማኔጅመንቱን በጋራ ለማስተዳደር ከመንግሥት እየተደራደረ ያለው፣ አንድ የቻይና ኩባንያ መሆኑን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡

እንደ ምንጮች ገለጻ ከሆነ መንግሥት የእዚህን ግዙፍ ተቋም የተወሰነ ድርሻ ለመሸጥ ጀመረ የተባለው ድርድር ያልተጠበቀ ሲሆን፣ ወደዚህ ሐሳብ የተገባበት ምክንያት ግልጽ አለመሆኑን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ወገኖች ይገልጻሉ፡፡ ድርድሩም በከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የተያዘ ስለመሆኑ የሚጠቁመው የምንጮች መረጃ፣ በተለይ ከ60 ዓመታት በላይ የቆየውን የመርከብ አገልግሎት ዘርፍ ያጠቃልላል ተብሏል፡፡ ይህ ደግሞ በዚህ አገልግሎት ዘርፍ አገሪቱ ይዛ የቆየችውን ተጠቃሚነት ሊያሳጣት ይችላል የሚል ሥጋት እንደፈጠረባቸው የሚናገሩት ምንጮች፣ የሽያጭ ድርድሩ ከአጠቃላይ የኢንተርፕራይዙ ሀብት በመቶኛ ተሰልቶ የሚደረግ ነው ይላሉ፡፡

የኢንተርፕራይዙን የባለቤትነት ድርሻ በተወሰነ ደረጃ በሽያጭ የማዛወሩን ዕቅድ በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራናቸው የኢንተርፕራይዙ የሥራ ኃላፊዎች ደግሞ፣ ስለጉዳዩ ምንም መረጃ የሌላቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ሚኒስቴር ጉዳዩን በወሬ ደረጃ ከመስማት ውጪ የሚያውቀው ነገር አለመኖሩን ገልጿል፡፡

ይሁን እንጂ ከኢንተርፕራይዙ የባለቤትነት ድርሻ ላይ የተወሰነውን ለማስተላለፍ ንግግሮች እየተደረገ ስለመሆኑ የተለያዩ ወገኖች እየገለጹ ሲሆን፣ ይመለከታቸዋል የተባሉ አካላት በጉዳዩ እንዳይሳተፉ መደረጋቸውንም ይጠቁማሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት እንደ ቴሌ፣ አየር መንገድና ባንኮች ሁሉ ኢንተርፕራይዙ የውጭ ኩባንያን ለማስገባት ፍላጐት እንዳልነበረው ቢገመትም፣ አሁን የ40 በመቶ የባለቤትነት ድርሻውን ለማስተላለፍ ተደረሰበት የተባለው ደረጃ አስፈላጊነቱ ላይ ጥያቄ የሚያቀርቡ ወገኖች አሉ፡፡

ኢንተርፕራይዙ በሥሩ የኢትዮጵያ ንግድ መርከብን፣ የኢትዮጵያ ደረቅ ወደብ አገልግሎትን፣ የማሪታይምና በቅርቡ ግዙፉን የትራንስፖርት ድርጅት ኮሜት ትራንስፖርት አገልግሎትን አጠቃሎ የያዘ ነው፡፡ በአትራፊነቱ የሚጠቀስ የመሆኑን ያህል አገራዊ ምልክትም በመሆኑ ከመንግሥት ባለቤትነት መውጣት አይኖርበትም በማለት የሚከራከሩ አሉ፡፡ በእርግጥ የአገልግሎት አሰጣጡን ለማቀላጠፍ ከሆነ ማኔጅመንቱን በተወሰነ ደረጃ መስጠት እየተቻለ፣ ለምን ወደዚህ ሐሳብ እንደተገባ ግልጽ አለመሆኑን የሚገልጹም አልጠፋም፡፡ በ2008 በጀት ዓመት ብቻ ከ1.3 ቢሊዮን ብር ትርፉ እንዳስመዘገበ የሚጠቁሙት መረጃዎች በየዓመቱ ትርፍ እያደገ መምጣቱን ያስረዳሉ፡፡

ኢንተርፕራይዙ በ2008 በጀት ዓመት ብቻ ወደ 17 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ያስገባ ሲሆን፣ ይህ ገቢ ከቀደሙት ዓመታት ጋር ሲነፃፀር በየዓመቱ እያደገ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ኢንተርፕራይዙ በአምስት ዋና ዘርፎች የተከፋፈሉ አገልግሎቶችን የሚሰጥ በመሆኑ፣ ከእነዚህ ውስጥ በተለይ የመርከብ ዘርፍን የባለቤትነት ድርሻ ማካፈል ላይ ከተደረሰ አገራዊ ጉዳቱ ያመዝናል በማለት ሥጋታቸውን የሚናገሩ አሉ፡፡ በተለይ ኢንተርፕራይዙ ከሚያገኘው ገቢ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው ከመርከብ ዘርፍ አገልግሎት መሆኑ ደግሞ፣ የመርከብ ዘርፉን የባለቤትነት ድርሻ ማስተላለፍ በአገር ገቢ ላይም ተፅዕኖ እንዳለው ተጠቁሟል፡፡  

የኢትዮጵያን የወጪና የገቢ ንግድ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዋጋ በሚወስኑ የመርከብ አጓጓዦች እጅ እንዳይወድቅ፣ አገሪቱ ለአገልግሎቱ ከፍተኛ የሆነ ወጪ እንዳታወጣ ያገዛት የራሷ መርከቦች ባለቤት በመሆኗም ጭምር መሆኑንም ያወሳሉ፡፡

ከ60 ዓመታት በላይ የዘለቀው የንግድ መርከብ አገልግሎት በውጭ ተቋማት ሥር ከወደቀ አገራዊውን ጥቅም ሊጎዳ ይችላል የሚል ሥጋት ያላቸው ወገኖች፣ በዚህ ዘርፍ አገሪቷ ይዛ የቆየችውን ጥንካሬ ሊያሳጣት እንደሚችልም ሥጋታቸውን ይጠቁማሉ፡፡ ዛሬ የባህር በር ከሌላቸው አገሮች የራሷን መርከቦች በመጠቀም የገቢና የወጪ ዕቃዎችን በማስተናገድ የምትታወቅ ሲሆን፣ በተለይ ገቢ ዕቃዎችን ከውጭ ኩባንያዎች ተፅዕኖ ውጪ ለማስገባት መቻሏ በራሱ ለኢኮኖሚውም ትልቅ ጥቅም አለው በማለትም ያስረዳሉ፡፡

ኢትዮጵያ አሁንም ሆነ ቀደም ብሎ በራስዋ መርከቦች መገልገል በመቻሏ፣ በቀይ ባህር አካባቢ በተለያዩ ጊዜያት የሚፈጠሩ ቀውሶች የመርከብ አገልግሎት ዋጋን በሚያንሩበት ወቅት ተጠቃሚ ሲያደርጋት ቆይቷል፡፡ አሁንም አንዳንድ ቦታዎች ላይ የሚታዩ ውጥረቶች በተከሰቱ ቁጥር የመርከብ አገልግሎት ዋጋ ሲጨምር፣ ኢትዮጵያ በራስዋ መርከብ ማጓጓዝዋ ከከፍተኛ ወጪ ስለሚያድናት የመርከብ ዘርፍን ባለቤትነት ድርሻ ማካፈል ጎጂ ሊሆን ይችላል የሚል ሐሳብ ይሰማል፡፡

በሌላ በኩል ግን የንግድ መርከቡን ዘርፍ የባለቤትነት ድርሻ ማስተላለፍ ከጉዳቱ ጥቅሙ ያመዝናል የሚል አቋም ያላቸው ወገኖች ደግሞ፣ እንዲያውም መንግሥት ዘግይቷል የሚል እምነት አላቸው፡፡ የአገሪቱ የገቢ ዕቃዎች በኢንተርፕራይዙ ብቻ እንዲስተናገዱ የሚያስገድድ በመሆኑ፣ ለገቢ ዕቃዎች ኢንተርፕራይዙ የሚያስከፍለው የማጓጓዣ ዋጋ ከፍተኛ መሆን የገቢ ዕቃዎች ዋጋ እንዲንር አንድ ምክንያት እንደነበር ይጠቁማሉ፡፡

ኢንተርፕራይዙ ለሚያጓጉዛቸው ዕቃዎች የሚጠይቀው ዋጋ ፈጽሞ ከሌሎች ጋር እንደማይገናኝ የሚጠቁሙት እነዚህ ወገኖች፣ የባለቤትነት ድርሻውን ካከፈለ ግን በውድድር የሚስተናገድ በመሆኑ በአማራጭነት ተገልጋዮች ሊጠቀሙ ይችላሉ ይላሉ፡፡ የባለቤትነት ድርሻ በውስጡ አስገዳጅ ነገሮችን ያስቀራል የሚል እምነትም አላቸው፡፡  

ኢንተርፕራይዙ በአሁኑ ወቅት 11 አዳዲስ የሚባሉ መርከቦች ያሉት ሲሆን፣ በዓመት የጭነት ማመላለስ አቅሙን ከአምስት ሚሊዮን ቶን በላይ አድርሷል፡፡ ከ220 በላይ መዳረሻዎች ያሉት የአገሪቱ የመርከብ አገልግሎት 60 በመቶ የሚሆነውን ወጪና ገቢ ዕቃዎች ያጓጉዛል፡፡ ቀሪውን ደግሞ ከሌሎች የመርከብ ድርጅቶች በኪራይና በሽርክና አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ኢንተርፕራይዙ በአሁኑ ወቅት በሥሩ ከ260 በላይ የዕቃ ማጓጓዣ ተሽከርካሪዎች አሉት፡፡ ሰባት የደረቅ ወደቦችን ያስተዳድራል፡፡ የኢንተርፕራይዙ አጠቃላይ ሀብት ከ20 ቢሊዮን ብር በላይ ይገመታል፡፡         

Standard (Image)

የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን መዋቅራዊ ለውጡን ይፋ አደረገ

$
0
0

- ለአቃቂ ቃሊቲ መንገድ ግንባታ የዲዛይን ለውጥ ሊደረግ ነው

የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን በአደረጃጀቱ ላይ መዋቅራዊ ለውጥ ማድረጉን ይፋ አደረገ፡፡ ለውጡንም ተከትሎ የአመራር ለውጦችን በማካሄድ የተለያዩ ክፍሎች ኃላፊዎችም መነሳታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የባለሥልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኝ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የከተማዋን የመንገድ አገልግሎት ማሻሻልን ዓላማ ያደረገ የመዋቅር ተደርጓል፡፡ የመዋቅር ለውጡ ካካተታቸው ውስጥ ቀድሞ በአንድ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበረው አሠራር፣ ወደ አራት ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጆች እንዲያድግ ተደርጓል፡፡ እንዲሁም በርከት ያሉ አዳዲስ የሥራ ክፍሎች የተከፈቱ ሲሆን፣ እያንዳንዳቸውም በዳይሬክቶሬት እንደሚመሩ ዋና ሥራ አስኪያጁ አስረድተዋል፡፡

ከአንድ ወደ አራት ብዛታቸው ያደገው ምክትል ሥራ አስኪያጆችም በዋናነት የየራሳቸውን የሥራ ዘርፍ ያስተባብራሉ ተብሏል፡፡ እነዚህም የመንገድ ሀብት አስተዳደር፣ የምህንድስና ጨረታ፣ ኮንትራትና የጥናት ክፍል፣ በራስ ኃይል የመንገድ ግንባታና የሰው ኃይልና የፋይናንስ አስተዳደር ናቸው፡፡

ከባለሥልጣኑ ኃላፊነት የተነሱ ግለሰቦችን አስመልክቶ ዝርዝር ማብራሪያ ባይሰጡም፣ በርካታ የሥራ ክፍሎች በአዲስ ሠራተኞችና አመራሮች እንዲተኩ መደረጋቸውንም ዋና ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡

በቅርቡ ባለሥልጣኑ በአንድ ማዕከል የነበረውን አሠራሩን ወደ አምስት ዲስትሪክቶች በማስፋት እንቅስቃሴ መጀመሩን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

በተያያዘ ዜናም ባለሥልጣኑ በቅርቡ እንደሚያስገነባቸው ከሚጠበቁ መንገዶች መካከል የአቃቂ-ቃሊቲ-ቂሊንጦ መንገድ አንዱ ነው፡፡ ከአሥር ዓመት በፊት ተዘጋጅቶ የነበረውን ዲዛይን እንደገና ለማሻሻል ዝግጅት ማድረጉን አስረድተዋል፡፡

ከቻይና ኢግዚም ባንክ በተገኘ 102.7 ሚሊዮን ዶላር ብድር ባለሥልጣኑ በሁለት ምዕራፍ ከሚያስገነባቸው መንገዶች አንዱ ከቃሊቲ ቀለበት መንገድ አደባባይ እስከ ቱሉ ዲምቱ የሚገኘው ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ ከቃሊቲ ቀለበት መንገድ በቡልቡላ እስከ ቂሊንጦ አደባባይ ያለው መንገድ ነው፡፡

ነገር ግን ከቃሊቲ እስከ ቱሉ ዲምቱ የሚገኘው መንገድ ቀደም ብሎ የተሠራለት ዲዛይን ቢኖርም፣ በኋላ በርካታ የአገልግሎት መስጫ መሠረተ ልማቶች የተገነቡ በመሆናቸው፣ እነዚህን ታሳቢ ያደረገ የዲዛይን ለውጥ እንደሚደረግለት ዋና ሥራ አስኪያጁ አስታውቀዋል፡፡

ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ከተደረገ በኋላ የዲዛይን ማሻሻያው በስድስት ወራት ውስጥ ሊጠናቀቀ እንደሚችል፣ ኢንጅነር ሀብታሙ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

 

Standard (Image)

በመልሶ ማልማት የተፈናቀሉ ነጋዴዎች ቃል የተገባልንን መሬት ማግኘት አልቻልንም አሉ

$
0
0

ከመሀል አዲስ አበባ በመልሶ ማልማት ፕሮግራም የተፈናቀሉ ነጋዴዎች ግንባታ የሚያካሂዱበት ምትክ ቦታ እስካሁን ድረስ ስላልተሰጣቸው ለከፍተኛ ችግር መዳረጋቸውን፣ ለግንባታ ያዋጡት ገንዘብም ለዓመታት ያለሥራ መቀመጡን ገለጹ፡፡

ከአሥር በላይ በሚሆኑ አክሲዮን ማኅበራት ተደራጅተው የሚገኙ ከአንድ ሺሕ በላይ ነጋዴዎች፣ ጉዳያቸውን ለማስፈጸም ላለፉት ሦስት ዓመታት ቢመላለሱም ሰሚ ባለማግኘታቸው ምሬታቸውን እየገለጹ ነው፡፡

አቤቱታ እያቀረቡ የሚገኙት አክሲዮን ማኅበራት በልደታ ክፍለ ከተማ ሦስት፣ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ስምንት፣ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ሦስት ናቸው፡፡

በልደታ ክፍለ ከተማ ተክለሃይማኖት (ሰንጋ ተራ ቁጥር ሦስት) 33 ሔክታር መሬት ላይ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች በልማት ምክንያት ተነስተዋል፡፡ ከዚህ ቦታ ላይ የተነሱ 122 ነጋዴዎች ‹‹ጥቁር አንበሳ አክሲዮን ማኅበር›› በሚባል ስያሜ የንግድ ድርጅት አቋቁመዋል፡፡

ነጋዴዎቹ የተነሱት በ2006 ዓ.ም ቢሆንም፣ የከተማ ቦታ በሊዝ ስለመያዝ የወጣው አዋጅ ቁጥር 721/2004 የሚፈቀድላቸውን ቦታ ማግኘት እንዳልቻሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የጥቁር አንባሳ አክሲዮን ማኅበር ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ አበበ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ይነግዱበት የነበረውን ቦታ ከለቀቁ ሦስት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ 122 የሚሆኑት የአክሲዮን ማኅበሩ አባላት በሚሰጣቸው ቦታ ላይ ግንባታ ለማካሄድ 24 ሚሊዮን ብር በማዋጣት በባንክ አስቀምጠው ቢጠባበቁም፣ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አገልግሎት ማግኘት አልቻሉም፡፡

በሊዝ አዋጁ ከመልሶ ማልማት ቦታዎች የሚነሱ ነጋዴዎች በተለይም የቀበሌ ወይም የመንግሥት የንግድ ቤት ተከራዮች፣ በአማካይ በነፍስ ወከፍ 25 ካሬ ሜትር እንዲሰጣቸው ተፈቅዷል፡፡ ነገር ግን ይኼ ድንጋጌ ተፈጻሚ መሆን ባለመቻሉ ቅሬታ እየተፈጠረ ይገኛል፡፡

ለችግር መዳረጋቸውን ከሚገልጹ ሌሎች አክሲዮን ማኅበራት መካከል ‹‹ተደንጓ የመልሶ ማልማት አክሲዮን ማኅበር›› ይገኝበታል፡፡ ይህ ሥፍራ የሚገኘው ከዋቢ ሸበሌ ሆቴል ጀርባ በሚገኘው የመልሶ ማልማት ፕሮግራም ቦታ ሲሆን በጠቅላላው 10.6 ሔክታር ይሸፍናል፡፡ ከዚህ ቦታ ላይ የተፈናቀሉ 124 ነጋዴዎች ላቋቋሙት አክሲዮን ማኅበር 19 ሚሊዮን ብር አዋጥተው፣ ቦታውን ላለፉት ሦስት ዓመታት መጠበቃቸውን ይናገራሉ፡፡

ነገር ግን ቦታውን ማግኘት ባለመቻላቸው ለተለያዩ ችግሮች እንደተዳረጉ፣ አንዳንድ የአክሲዮን ማኅበሩ አባላት ከንግድ ሥራ ውጪ መሆናቸውም እየተገለጸ ነው፡፡

የተደንጓ የመልሶ ማልማት አክሲዮን ማኅበር ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ዓብይ ገብረ ዮሐንስ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ቦታውን በወቅቱ ተረክበው ግንባታ ማካሄድ ባለመቻላቸው በርካታ የአክሲዮን አባላት ለከፍተኛ ችግር እየተዳረጉ ነው፡፡

ከአዲስ አበባ መሬት ልማትና ከተማ ማደስ ኤጀንሲ የተገኘ መረጃ እንደሚጠቁመው፣ በአካባቢው ሲካሄድ የቆየው የአካባቢ ልማት ፕላን (LDP) በወቅቱ ተጠናቆ፣ ሽንሻኖ በማካሄድ ወደ ልማት ማስገባት አልተቻለም፡፡

‹‹በአሁኑ ወቅት ግን የአካባቢ ልማት ፕላን የተጠናቀቀ በመሆኑ በቅርቡ ለአክሲዮን ማኅበራቱ ቦታ ማስረከብ ይጀምራል›› ሲሉ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የኤጀንሲው ባለሙያ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ 

Standard (Image)

ሐበሻ ሲሚንቶ ከወር በኋላ ማምረት እጀምራለሁ አለ

$
0
0

ሐበሻ ሲሚንቶ አክስዮን ማኅበር ሆለታ አካባቢ በ30 ሔክታር ቦታ ላይ ከ155 ሚሊዮን ዶላር በሚበልጥ ወጪ እያከናወነ ያለው የሲሚንቶ ፋብሪካ ግንባታ 95 በመቶ በመጠናቀቁ በሚቀጥለው ወር የሙከራ ምርት፣ ከሁለት ወራት በኋላ ደግሞ ሙሉ በሙሉ ማምረት እንደሚጀምር አስታወቀ፡፡

የሐበሻ ሲሚንቶ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን አቢ (ኢንጂነር) እንደገለጹት፣ ከተጠናቀቁት የግንባታ ሥራዎች መካከል የድንጋይ ከሰል፣ በተጓዳኝነት የቀይ አፈር፣ የኖራ ድንጋይና ፑሚስ የሚባሉት ጥሬ ዕቃዎች የሚከማችባቸው እያንዳንዳቸው 240 ሜትር በ44 ሜትር ስፋት ያላቸው ሦስት ትልልቅ መጋዘኖች ግንባታዎች ይገኙበታል፡፡

እያንዳንዳቸው ስድስት ሺሕ ቶን ወይም በአጠቃላይ 24 ሺሕ ቶን የመያዝ አቅም ያላቸው አራት የሲሚንቶ ማጠራቀሚያ ጋኖች ግንባታም ተጠናቋል፡፡ የፋብሪካው ግንባታ ከሚካሄድበት ሁለት ኪሎ ሜትር ያህል ወጣ ብሎ በሚገኝ ሥፍራም፣ ከ200 ሜትር በላይ ጥልቀት ያለው ጉድጓድ ተቆፍሮ የወጣው ውኃም ለፋብሪካው አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ተገልጿል፡፡

አቶ መስፍን እንደሚሉት፣ ከቀሩት አምስት በመቶ ሥራዎች መካከል የፋብሪካውን መሣሪያዎች መፈተሽና ጊዜያዊ ርክክብ ማካሄድ ይገኝበታል፡፡ በመሣሪያዎቹ ላይ ፍተሻ የማካሄድ ሥራ ተጀምሮ አብዛኞቹ ተፈትሸው ጥሩ ይዞታ ላይ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡

ዘመናዊ የጥራት ማረጋገጫ መሣሪያ፣ እንዲሁም 18 ሺሕ ቶን የሚጠጋ የድንጋይ ከሰል፣ ሦስት ሚሊዮን የሲሚንቶ ማሸጊያ ከረጢትና 900 ሺሕ ዶላር የሚያወጡ ልዩ ልዩ መለዋወጫዎች መገዛታቸውንም አቶ መስፍን አስረድተዋል፡፡

ፋብሪካውን ከሌሎች መሰል ፋብሪካዎች ለየት የሚያደረገው ምንድነው? ተብለው የተጠየቁት ጥያቄ አቶ መስፍን፣ እስካሁን ያሉት የሲሚንቶ ፋብሪካዎች በአብዛኛው በግል ባለሀብቶችና በጥቂት ባለድርሻዎች የተያዙ መሆናቸውን በማስታወስ፣ ሐበሻ ሲሚንቶ ፋብሪካ ግን ከ16 ሺሕ 500 በላይ ባለአክሲዮኖች የተሳተፉበት በመሆኑ ለየት ይላል ብለዋል፡፡

አሁን ባለው የገበያ ሁኔታ የሲሚንቶ አቅርቦትና ፍላጎት እየጨመረ መሆኑን በተመለከተ፣ የፍላጎቱን ያህል አቅርቦቱ ባለመጨመሩ ምክንያት ፋብሪካው ሳይቸገር ወደ ገበያ እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡ በዚህም ከ38 በላይ አከፋፋዮችና ነጋዴዎች ከአክሲዮን ማኅበሩ ጋር አብረው ለመሥራት ፍላጎት እንዳሳዩም ተናግረዋል፡፡

እንደ አቶ መስፍን ማብራሪያ፣ ሲሚንቶ ለውጭ ገበያ የማቅረቡን ጉዳይ  አክሲዮን ማኅበሩ በቢዝነስ ዕቅዱ ውስጥ አስገብቶታል፡፡ በዚህ መሠረት በአገር ውስጥ ያለው የገበያ ድርሻ ከታወቀ በኋላ በሚቀጥለው ዓመት ወደ ጎረቤት አገሮች በተለይም ወደ ኬንያና ደቡብ ሱዳን ለማቅረብ ጥናት በመካሄድ ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡

ፋብሪካው አሁንም በፕሮጀክት ደረጃ ላይ ቢሆንም የኮርፖሬት ማኅበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት ለአካባቢው ማኅበረሰብ ንፁህ የመጠጥ ውኃ አቅርቦት፣ የጥሬ ዕቃ ማውጫ ቦታ ላይ ለተቋቋመው የመንግሥት ክሊኒክ በፀሐይ ኃይል የሚሠራ የኤሊክትሪክ ኃይል የማስገባትና ሕዝብ በብዛት የሚንቀሳቀስባቸውን የውስጥ ለውስጥ መንገዶች የመጥረግና የማስተካከል ሥራዎች ማከናወኑም ተገልጿል፡፡

የፕሮጀክቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዬ አዳነ እንደገለጹት ፋብሪካው ሥራውን ሲጀምር በቀን 30 ሺሕ ኩንታል ወይም ሦስት ሺሕ ቶን ኦፒሲ፣ እንዲሁም 45 ሺሕ ኩንታል ፒፒሲ ሲሚንቶ የማምረት አቅም የሚኖረው ሲሆን፣ ወደፊትም አብዛኛው ሕዝብ የሚጠቀምበትን 22.5 የተባለውን ሲሚንቶ ለማቅረብ ሐሳብ አለው፡፡

ፋብሪካዎች ማውጣት ያለባቸው የብክለት ልቀት መጠን የዓለም ባንክ ባወጣው መሥፈርት መሠረት 50 ሚሊ ግራም ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ደግሞ ያስቀመጠችው መሥፈርት ከፍተኛው 150 ሚሊ ግራም ነው፡፡ ከዚህ አኳያ የሐበሻ ሲሚንቶ ፋብሪካ የሚያወጣው የብክለት ልቀት መጠን ከፍተኛው 30 ሚሊ ግራም እንደሆነና ይህም ከወጡት መሥፈርቶች ያነሰ እንደሚሆን ሥራ አስኪያጁ አስረድተዋል፡፡

የፕሮጀክቱ የኤሌክትሪካልና የኢንስትሩመንት ኃላፊ አቶ ቴዎድሮስ ኃይለ ማርያም፣ ፋብሪካው 25 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል እንደሚያስፈልገው፣ ለዚህም የሚሆን የሰብስቴሽንና የኃይል ማሰራጫ ግንባታዎች መጠናቀቃቸውን ገልጸዋል፡፡ ከገፈርሳ ግድብ ወደ ሙገር ከሚሄደው 132 ኪሎ ቮልት ኃይል ተሸካሚና አስተላላፊ መስመር 15 ሜጋ ዋት ኃይል እንዲጠቀም እንደተፈቀደለትም ሥራ አስኪያጁ አክለዋል፡፡

Standard (Image)

በደካማ የሥራ አፈጻጸም የተገመገሙ ሁለት ኤጀንሲዎች ተዋህደው አዲስ መሥሪያ ቤት ተቋቋመ

$
0
0

በደካማ የሥራ አፈጻጸም ሲወቅሱ የቆዩት የሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲና  የግብርና ኢንቨስትመንትና መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ ተዋህደ፣ ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የሆነ መሥሪያ ቤት ተቋቋመ፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ኢንቨስትመንትና መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ ከክልሎች በውክልና ወስዶ ሲያስተዳድር የቆየውን መሬት እንዲመልስ የተወሰነ በመሆኑ፣ አዲሱ መሥሪያ ቤት መሬት የማስተዳደር ሥልጣን አይኖረውም፡፡ አዲስ የተቋቋመው ‹‹የሆርቲካልቸርና ግብርና ኢንቨስትመንት ባለሥልጣን›› የተሰኘው መሥሪያ ቤት ባለሀብቶችን መከታተልና መደገፍ ላይ ያተኩራል ተብሏል፡፡

እነዚህ ሁለት ኤጀንሲዎች በአገሪቱ የግብርና ዕድገት በተለይ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በአበባ፣ በጥርጣሬ፣ በቅባት እህሎች እንዲሁም በጥጥ ልማት ትልቅ ለውጥ ያመጣሉ ተብለው የተቋቋሙ ነበሩ፡፡

ነገር ግን ብዙ የተባለለት አበባም ሆነ የእህል ምርት እምብዛም ሆኖ ቀርቷል፡፡ በዚህ ምክንያት የዘርፉ ዋነኛ ተዋናዮች ባገኙት አጋጣሚ መሥሪያ ቤቶቹን ከመውቀሳቸውም በተጨማሪ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትም በሥራ አፈጻጸም ደካማነታቸው ወቅሰዋቸዋል፡፡

የእነዚህን ኤጀንሲዎች ድክመት በመለየት ዘርፉን በሚገባው ደረጃ ለመደገፍ አዲስ መዋቅር ሲጠና ቆይቶ በታኅሳስ ወር አጋማሽ ባለሥልጣኑ ተቋቁሟል፡፡ ነገር ግን የመዋቅር ለውጥ ጥናቱ የተካሄደበት መንገድ ያጠራጠራቸው ባለሙያዎች፣ ጊዜው ሳይረፍድ ጥናቱ በትክክለኛ ባለሙያዎች ሊከለስ ይገባል የሚል አስተያየት እየሰጡ ነው፡፡

ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የዘርፉ ባለሙያ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ይህ ጥናት የተካሄደው በሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲ የቀድሞ ዋና ዳይሬክተርና የግብርና ኢንቨስትመንት መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ የቀድሞ ዋና ዳይሬክተር የበላይነት ነው፡፡

‹‹እነዚህ አመራሮች ተወቃሽ እንደ መሆናቸው ጥናቱ በድጋሚ ሊታይ ይገባል›› ሲሉ እኝሁ ባለሙያ ይገልጻሉ፡፡

በተካሄደው ጥናት ከዚህ በፊት በሁለቱ የግብርና ዘርፎች የተፈጠሩ ችግሮች ተለይተው የመፍትሔ አቅጣጫ ተመላክቷል ወይ? ለተፈጠረው ችግርስ ተጠያቂ አካል ተለይቷል ወይ?›› በማለት የሚጠይቁ ባለሙያዎች አሉ፡፡

አዲሱ ባለሥልጣን መሥሪያ ቤት አዲስ አመራር ተሰይሞለታል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስተር ጽሕፈት ቤት አቶ ያዕቆብ ያላን ዋና ዳይሬክተር፣ አቶ አበራ ሙላትን ደግሞ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አድርጎ ታኅሳስ 21 ቀን 2009 ዓ.ም. መሾሙ ታውቋል፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የንግድ ሚኒስትር የነበሩትን አቶ ያዕቆብ፣ የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አድርጎ ሾሞ ነበር፡፡

የኢንተርፕራይዙ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ የሆኑት የትራንስፖርት ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ በቅርቡ የሰበሰቡት ቦርድ፣ አቶ ያዕቆብ መንግሥት ሌላ ኃላፊነት እንደሚፈልጋቸው በመግለጽ ሹመቱ እንዲቀር መደረጉን አመልክተዋል፡፡ እስከዚያው ግን ኢንተርፕራይዙን አቶ መስፍን ተፈራ ተጠባባቂ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው እንዲሠሩ መመደባቸውን አቶ አህመድ አስታውቀዋል፡፡

የአዲሱ የሆርቲካልቸርና የግብርና ኢንቨስትመንት ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሆነው የተሸሙት አቶ አበራ፣ የባለሥልጣኑን መቋቋም ለሪፖርተር አረጋግጠዋል፡፡ ነገር ግን በይፋ መግለጫ የሚሰጥ በመሆኑ፣ ዝርዝር ውስጥ ከመግባት እንደሚቆጠቡ አክለዋል፡፡

Standard (Image)

የሰማያዊ ፓርቲ የቀድሞ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ መከላከያ ምስክሮቹን ማሰማት ጀመረ

$
0
0

በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥሮ የተከሰሰው የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ ሐሙስ ታኅሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. የመከላከያ ምስክሮቹን ማሰማት ጀመረ፡፡

የፍልስፍና ምሁሩን ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋንና የሕግ ሙሁሩን ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለ ማርያምን ጨምሮ አሥር መከላከያ ምስክሮች እንዳሉት ያስመዘገበው አቶ ዮናታን፣ የመከላከያ ምስክሮቹ ክሱን ለሚመረምረው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የምስክርነት ቃላቸውን ከመስጠታቸው በፊት የተከሳሽነት ቃሉን ሰጥቷል፡፡

ከፌስቡክ ጓደኞቹ ጋር ባደረጋቸው ውይይቶች የሰጣቸው አስተያየቶች እንደ ወንጀል ተቆጥረው ክስ እንደተመሠረተበት የተናገረው አቶ ዮናታን እንደ፣ ፖለቲከኛና ሐሳቡን በነፃነት እንደሚያራምድ ማንኛውም የኅብረተሰብ አካል ድርጊቱ ጥፋት ነው ብሎ እንደማያምን አስረድቷል፡፡ ባለው የፖለቲካ ኃላፊነት በፌስቡክም ሆነ በተለያየ መንገድ ማለትም ለመገናኛ ብዙኃንም ተመሳሳይ ሐሳብ እንደሚናገር የገለጸው አቶ ዮናታን፣ ዓቃቤ ሕግ ኅብረተሰቡን ለአመፅ የሚያነሳሳ ጽሑፍ እንዳሰራጨ አድርጎ ክስ ማቅረቡ ስህተት መሆኑን ተናግሯል፡፡ ምናልባት አለመረዳት ሊሆን እንደሚችልና ፍርድ ቤቱም ግንዛቤ ሊወስደው ይችላል የሚል እምነት እንዳለው አክሏል፡፡ የጻፈው ጽሑፍ ግን ለሕዝብ ቢደርስ ችግር እንደሌለውም ተናግሯል፡፡

በፌስቡክ ገጹ የጻፋቸው፣ የተወያየባቸውና ሐሳቡን ያካፈለባቸው መጣጥፎች መንግሥት ስለሶማሊያና ጋምቤላ በተደጋጋሚ የገለጻቸው ሐሳቦች እንደሆኑም አቶ ዮናታን ተናግሯል፡፡ ‹‹ሐሳቤን መግለጽ ካልቻልኩ፣ ካልተወያየሁ፣ ካልተናገርኩና ካልተቃወምኩ ታዲያ ለምን ፖለቲከኛ ሆንኩ?›› በማለት የጠየቀው አቶ ዮናታን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ይቅርታ በጠየቁበትና በኦሮሚያ ክልል የተፈጠሩ ሁከቶች በመልካም አስተዳደር ዕጦት መሆኑን በገለጹበት ጉዳይ፣ በእሱ ላይ ወንጀል ሆኖ መከሰሱ ተገቢነት እንደሌለው አስረድቷል፡፡

የተከሰሰው ከፌስቡክ ገጽ በወጣ ጽሑፍ እንጂ በኦሮሚያ በተደረገው ረብሻ እንዳልሆነና ዓቃቤ ሕግም ምንም ዓይነት ማስረጃ እንዳላቀረበ ገልጿል፡፡ ፌስቡክ የጓደኛን ልክ (ብዛት) ስለሚመጥን ዓቃቤ ሕግ በክሱ እንዳለው ሕዝብን ለማነሳሳት ገደብ እንዳላለፈ አስረድቷል፡፡

አቶ ዮናታን በዝርዝር የተከሳሽነት ቃሉን ከሰጠ በኋላ ጠበቃው ምስክሮቹ የሚመሰክሩበትን ጭብጥ አስይዘው እንደጨረሱ፣ ዶ/ር ያዕቆብ በቅድሚያ የሙያ ምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

የ72 ዓመቱ የሕግ ምሁር ዶ/ር ያዕቆብ ለፍርድ ቤቱ በሰጡት የሙያ ምስክርነት እንደገለጹት፣ አቶ ዮናታን የተከሰሰው በሽብር መሆኑን ያውቃሉ፡፡ ‹‹ክቡራን ዳኞች እንደሚያውቁት ሽብርተኝነት ከባድ ወንጀል ነው፡፡ ዓለም አቀፍ ወንጀል በመሆኑ ድርጊቱን የፈጸመ አካል የትኛውም አገር መክሰስ ይችላል፡፡ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤትም ሊያጠቃልለው በውይይት ላይ ነው፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ወደ ዮናታን ክስ ሲመለሱ ግን ከጥቂት ሰዎች ጋር በፌስቡክ መገናኘቱ የሽብር ወንጀል ነው ወይም ፈጽሟል ለማለት እንደሚከብድ ተናግረዋል፡፡ በአሜሪካ ናይን ኢለቨን (9/11) የተፈጸመውን የሽብር ተግባር ያስታወሱት ዶ/ር ያዕቆብ፣ በናይጄሪያ 200 ልጃገረዶች ከታገቱት፣ በኡጋንዳ፣ በኬንያና በተለያዩ አገሮች ከተፈጸሙት የሽብር ወንጀሎች አንፃር ዮናታን በፌስቡክ የሽብር ተግባር ፈጽሟል ማለት ‹‹ድርጊቱን ያሳንሰዋል›› ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያን ሕገ መንግሥት ድንጋጌንና ተቀብላ ያፀደቀቻቸውን የሰብዓዊና የዴሞክራሲ መብቶችንም የሚጥስ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የፌስቡክ ንግግር፣ ውይይትና ሐሳብ መስጠት ለሽብር አስተዋጽኦ ያደርጋል ማለት እንደሚከብድም ገልጸዋል፡፡ በእሳቸው እምነት አቶ ዮናታን በፌስቡክ የጻፈውና የተጻጻፈው በሕገ መንግሥቱ በተፈቀደው የንግግር ነፃነት ውስጥ የሚወድቅ መሆኑን  ነው፡፡ ሰውን የሚያዋርድ፣ ሕግን የጣሰና ባህልን የሚያንኳስስም እንዳልሆነ አክለዋል፡፡

ንግግር ተፈጥሯዊ ከመሆኑ አንፃር ያልተጠቀሰበት ዓለም አቀፋዊ የስምምነት ቃል ኪዳን ሰነድ እንደማይገኝም ጠቁመዋል፡፡ በእርግጥ ሐሳብን መግለጽ፣ መነጋገርና መጻፍ ፍፁም ስላልሆነ ገደብ እንዳለውም የገለጹት ዶ/ር ያዕቆብ፣ አቶ ዮናታን የጻፈው ግን በተከለከሉት ወይም ገደብ በተጣለባቸው ውስጥ እንደማይካተት አስረድተዋል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ያቀረበበትን ክስ ማንበባቸውንና እሳቸው እንደገባቸው ሐሳብን በነፃነት መግለጽ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ሁለተኛ መከላከያ ምስክር ሆነው የቀረቡት የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው ናቸው፡፡ ሐሳብን በነፃነት መግለጽ ምን ማለት እንደሆነ እንዲያስረዱ ተጠይቀው እንደገለጹት፣ ሐሳብን በነፃነት መግለጽ እንደሚቻል ኢትዮጵያ ለመጀመርያ ጊዜ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌ ሲረቀቅ በ1948 (እ.ኤ.አ.) አብራ አርቃቂ እንደነበረች አስረድተዋል፡፡ በ1953፣ በ1969 እና በ1982 (እ.ኤ.አ.) በተደረጉ የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ ጉባዔዎች ላይም ተሳታፊ እንደነበረችም አስረድተዋል፡፡

ንግግር በይዘቱ እንደማይፈተሽ የገለጹት ዶ/ር ዳኛቸው ማንም ሐሳቡን የመጻፍ፣ የማውጣት፣ የመሳተፍ፣ የማጋራትና የማቅረብ መብት እንዳለውና መንግሥትና ሕዝብም የማወቅ መብት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡ ሰዎች እርስ በርሳቸው ሐሳብ መለዋወጥና መወዳደር መብታቸው መሆኑንም አክለዋል፡፡ ዴሞክራሲ ድምፅ ይፈልጋል፡፡ የአቶ ዮናታንን ጽሑፍ ሲያነቡት (የክስ ቻርጁን) እምነቱን ማስቀመጡን ተገንዝበዋል፡፡ እሳቸው በመንግሥት ላይ ተፅዕኖ ለመፍጠር ስምንት ዓመታት መጻፋቸውንም ጠቁመዋል፡፡

ስህተት ወንጀል እንዳልሆነ፣ አቶ ዮናታን ሲሳሳት ስህተቱን መቀበል ወይም አለመቀበል መብት መሆኑን የገለጹት ዶ/ር ዳኛቸው፣ ስህተት የሚሆነው አቶ ዮናታን ከጻፈው ጽሑፍ ላይ ይወሰድና ሌላ ስህተት ሲፈጸም መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ከድርጊት ወደ ሽብር ይኬዳል እንጂ፣ ከሐሳብ ወደ ሽብር መሄድ ከፈረሱ ጋሪው እንዲሉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሐሳብ እንደማይወሰን፣ የመለመን፣ የማሞገሥና የመተቸት መብት የተፈቀደ መሆኑንና ይዘት ሊመዘን እንደማይቻል ገልጸዋል፡፡ አቶ ዮታናታንም የተጠቀመበት መሣሪያ በግል ሐሳብን መግለጽ በመሆኑ፣ ከንግግርና ከጽሕፈት የሚመጣን ስህተት ማገድ ሳይሆን መፍቀድ መሆኑን ብዙ ፈላስፎች የሚስማሙበት እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ በዮናታን ጽሑፎች ላይ ሞራል የሚነካ ነገር አለማየታቸውንም አክለዋል፡፡ ሪፖርተር በበዓል ምክንያት ማተሚያ ቤት እስከገባበት ሐሙስ ታኅሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ አቶ ዮናታን በመከላከያ ምስክርነት ካቀረባቸው አሥር ሰዎች የሁለቱን ብቻ መስተናገድ ችሏል፡፡ የቀሪዎቹን መከላከያ ምስክሮች ቃል ማካተት አልተቻለም፡፡

 

Standard (Image)

በሩብ ዓመት ብቻ ከውጭ ቱሪስቶች 872 ሚሊዮን ዶላር መገኘቱ ተገለጸ

$
0
0

- የኦሞና የነጭ ሳር ፓርኮች ድንበር በዚህ ዓመት ይከለላል ተብሏል

በ2009 ዓ.ም. የመጀመሪያ ሩብ ዓመት 872 ሚሊዮን ዶላር ከውጭ ቱሪስቶች ብቻ መገኘቱን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

በባህልና ቱሪዝም መስኮች ዙሪያ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን ለመመለስ ፓርላማ ሐሙስ ታኅሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ለመጀመሪያ ጊዜ የተገኙት የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሯ ዶ/ር ሒሩት ወልደ ማርያም፣ የቱሪዝም ዘርፍ ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰትን እየሳበ መሆኑንና የበለጠ ቢሠራበት አገሪቷ በሃይማኖት መጻሕፍት እንደምትገለጸው የቱሪዝም ገነት መሆን እንደምትችል ገልጸዋል፡፡

በቅርቡ በአዲስ አበባ በተካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) የማይዳሰሱ ቅርሶች ጉባዔ ላይ ብቻ፣ ከ800 በላይ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ተሳታፊዎች መገኘታቸውን ጠቁመዋል፡፡

በአጠቃላይ በመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ብቻ 223,032 ቱሪስቶች በኮንፈረንስ ቱሪዝም፣ በምርምርና በተለያዩ ምክንያቶች ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸውን ሚኒስትሯ ገልጸዋል፡፡

አንድ ቱሪስት በቀን ምን ያህል ወጪ ያወጣል? የሚል ራሱን የቻለ ዓለም አቀፍ የሥሌት ቀመር እንዳለው የገለጹት ዶ/ር ሒሩት፣ በዚህ ሥሌት መሠረት 872 ሚሊዮን ዶላር ያህል ገቢ ሊመጣ እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡

የአገር ውስጥ ቱሪስቶች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን የገለጹት ሚኒስትሯ፣ በተመሳሳይ የመጀመርያው ሩብ ዓመት ውስጥ ከ300 ሺሕ በላይ የአገር ውስጥ ቱሪስቶች እንደነበሩ ጠቁመዋል፡፡

የብሔራዊ ፓርኮችን ድንበር ከመከለል አንፃር ተቋማቸው ምን እየሠራ እንደሆነ የተጠየቁት ሚኒስትሯ፣ አገሪቷ ካሏት ስምንት ብሔራዊ ፓርኮች መካከል የስድስቱ ድንበር በድጋሚ ተከልሎ በሚኒስትሮች ምክር ቤት መፅደቁን አውስተዋል፡፡

ድንበሮቹን በድጋሚ መከለል ከክልሎች መሬትን የመጠቀም መብት ጋር የሚገናኝ በመሆኑ ጥንቃቄ የሚሻ ጉዳይ እንደሆነ፣ የስድስቱ ፓርኮች ድንበርም ከክልሎች ጋር በተደረገ ጥልቅ ውይይትና መግባባት መፈጸሙን ገልጸዋል፡፡

የኦሞና የነጭ ሳር ፓርኮች ከአንድ በላይ ክልሎችን ወሰን የሚነኩ በመሆናቸው የበለጠ ጥንቃቄ፣ በፓርኮቹ ውስጥ የሠፈሩትን ወደ ሌላ ቦታ ማዘዋወርና መጠለያ መገንባትም የሚጠይቅ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ የሁለቱም ፓርኮች አዲስ ድንበር በ2009 ዓ.ም. እንደሚከለል አስረድተዋል፡፡

 

Standard (Image)

መንግሥት የአገር ውስጥ የመርከብ ወኪሎችን በአግባቡ እንዲቆጣጠር ጥሪ ቀረበ

$
0
0

- የወጪ ንግድ ሸቀጦችን በጂቡቲ ወደብ በኮንቴይነር ለማሸግ ብቻ ከ100 ዶላር በላይ ይጠየቃል

- የመርከብ ጭነት አስተላላፊዎች ችግሩ የመንግሥት እንደሆነ ይገልጻሉ 

የወጪ ንግድ ሸቀጦችን በጂቡቲ ወደብ በኮንቴይነር ውስጥ አሽጎ ለመላክ በአንድ ኮንቴይነር 110 ዶላር የሚጠየቀው ወጪ ተገቢነት የለውም ያሉ የዘርፉ ባለሙያዎች፣ ለዚህ ድርጊት አስተዋጽኦ ያደርጋሉ ያሏቸውን የውጭ መርከብ ኩባንያዎችን በመወከል    በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ወኪሎችን መንግሥት በአግባቡ እንዲቆጣጠር ጥሪ አቀረቡ፡፡

ሪፖርተር ያነጋገራቸው ምንጮች እንዳብራሩት፣ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ የባዶ ኮንቴይነር እጥረት ባይኖርም ባዷቸውን ወደ ጂቡቲ ለሚጓጓዙ ኮንቴይነሮች የሚከፈለው የትራንስፖርት ወጪ ሳያንስ፣ ወደ ጂቡቲ ወደብ የሚላኩ ሸቀጦችን በኮንቴይነር ውስጥ ለመጫን የሚከፈለው 110 ዶላር አግባብነት የጎደለው ነው ብለዋል፡፡ እንዲሁም በጂቡቲ የሚገኙ የመርከብ ወኪሎች የሚያስከፍሉት ታሪፍ በመሆኑ፣ ምርቶቹን እዚሁ በማሸግ መላክ እንዲቻል መንግሥት በተለይም ዘርፉን የሚቆጣጠረው የማሪታይም ጉዳዮች ባለሥልጣን፣ የበላይ የሆነው የትራንስፖርት ሚኒስቴርና ሌሎችም የመንግሥት አካላት ትኩረት እንዲሰጡበት ጠይቀዋል፡፡

የወጪ ንግድ ሸቀጦች ወደ ውጭ ሲላኩ በአገር ውስጥ ሳሉ በኮንቴይነር ባለመታሸጋቸው ምክንያት ከሚወጣባቸው የውጭ ምንዛሪ ወጪ ባሻገር፣ ምርቶቹ እስከ ጂቡቲ ወደብ በመኪና ተጭነው ሲጓጓዙ የሚደርስባቸውን የሥርቆት ወንጀል (ቅሸባ) ለማስቅረት የሚቻልባቸው ዕድሎች እየታጡ እንደሚገኙ የዘርፉ ተዋናዎች ይናገራሉ፡፡ ከዚህ ባሻገር በላኪና በምርት ተቀባይ መካከል ብዙውን ጊዜ ንትርክ የሚያስነሳውን የክብደት መቀነስ ችግርም ለመቀነስ እንደሚረዳ ተጠቅሷል፡፡ ወጪ ሸቀጦች በአገር ውስጥ በኮንቴይነር ታሽገው ቢወጡ ያላግባብ የሚወጣውን የውጭ ምንዛሪ ከማስቀረት በተጨማሪ (በብር የሚከፈል በመሆኑ)፣ የሸቀጦች ደኅንነትና የጥራት ደረጃ  በአግባቡ ተፈትሾና ተረጋግጦ እንዲወጣ ለማድረግ እንደሚያስችል ባለሙያዎቹ ይገልጻሉ፡፡

በየዓመቱ ከ200 እስከ 300 ሺሕ ቶን የሚገመት የቡና ምርት፣ እንዲሁም ከ300 እስከ 400 ሺሕ ቶን የሚገመቱ የቅባትና ጥራጥሬ እህሎችና ቅመማ ቅመሞች ወደ ውጭ እንደሚወጡ ሲገመት፣ ከዚህ ውስጥ እስከ 90 በመቶው ጂቡቲ ወደብ ከደረሱ በኋላ በኮንቴይነር እንደሚጫኑ ይገለጻል፡፡  

የኢትዮጵያ የመርከብ ጭነት አስተላላፊዎችና የመርከብ ኩባንያ ወኪሎች ማኅበር ፕሬዘዲንትና የማክፋ ቢዝነስ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሙሉጌታ አሰፋ ስለጉዳዩ በሪፖርተር ተጠይቀው ችግሩ መኖሩን ገልጸዋል፡፡ ምርቶች በአገር ውስጥ በኮንቴይነር ውስጥ እንዲጫኑ ቢደረግ የተዘረዙት ጠቀሜታዎች እንዳሉ ገልጸው፣ ለወጪ ሸቀጦች የሚውል ኮንቴይነር በአግባቡ አቀናጅቶ የማቅረብ ችግር ከፍተኛ በመሆኑ፣ የመርከብ ወኪሎች ኮንቴይነር ለማቅረብ እየተቸገሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

ማኅበሩ ይህንን ችግር እንዲፈታና ምርቶችም በአገር ውስጥ በኮንቴይነር ታሽገው የሚቀመጡበትን ቀልጣፋ አሠራርና ቅንጅት እንዲፈጥር ሲወተውት ቢቆይም ምላሽ እንዳላገኘ አቶ ሙሉጌታ ገልጸዋል፡፡ ከዚህም በላይ መንግሥት ለሌሎች ዘርፎች የሚሰጠውን ማበረታቻና ከቀረጥ ነፃ ዕድል ለጭነት አስተላላፊዎችም ሆነ ለመርከብ ወኪሎች ባለመስጠቱ ዘርፉን ችላ ለማለቱ አስረጂ አድርገውታል፡፡ በመሆኑም መሬት በተመጣጣኝ የሊዝ ዋጋ ቢያቀርብና የመርከብ ኩባንያዎችና ወኪሎች የኮንቴይነር ማከማቻዎችን እንዲገነቡ ቢያስችል፣ የኮንቴይነር መጫኛና ማውረጃ መሣሪያዎችን ከቀረጥ ለማስገባት እንዲቻል ቢፈቅድ፣ ባዶ ኮንቴይነር ወደ ጂቡቲ መላክ ሊቀንስ የሚያስችሉ መፍትሔዎች እንደሚሆኑ አቶ ሙሉጌታ ጠቅሰዋል፡፡

በዘርፉ ልምድ ያካበቱ ባለሙያዎች በአገር ውስጥ መርክብ ወኪሎች ላይ ከሚያቀርቡት የሰላ ትችት መካከል ‹‹የወኪል ወኪል›› ሆነው የሚሠሩ፣ ዋናዎቹ ወኪሎች በእጅ አዙር የሚያሽከረክሯቸው በመሆናቸው ለላኪዎች ተገቢውን አገልግሎት በመስጠት ኃላፊነታቸውን ከመወጣት ይልቅ የሚያጉላሉና አላስፈላጊ ወጪ የሚያስከትሉ ሆነዋል በማለት የሚያሰሙት ይገኝበታል፡፡ መንግሥት ትክክልኛ ወኪሎች እነማን እንደሆኑ በማጣራት ቁጥጥር እንዲያደርግ ጠይቀዋል፡፡

በሌላ በኩል አቶ ሙሉጌታ እንደሚከራከሩት፣ የወኪል ወኪል ወይም የሦስተኛ ወገን ሆኖ መሥራት በኢትዮጵያ ብቻም ሳይሆን በመላው ዓለም የሚሠራበት የተለመደ አሠራር ከመሆኑ ባሻገር፣ የአገር ውስጥ ወኪሎች ትክክለኛና ሕጋዊ አሠራርን ተከትለው ይሠራሉ፡፡ ይህንን የማያደርጉ ካሉና ያላግባብ ዋጋ የሚያንሩ ከሆነ ግን መንግሥት ተከታትሎ ዕርምጃ መውሰድ እንደጠበቅበት ተናግረዋል፡፡ ያልተገባ ዋጋ የሚጠይቁ የመርከብ ወኪሎች አሉ ቢባል እንኳ ጭነቱን የሚሰጣቸው ላኪ አንዱን የመርከብ ድርጅት ከሌላው አወዳድሮ የሚመርጥ በመሆኑ፣ እንዲህ ያለው ትችት ብዙም እንደማያስኬድ ገልጸዋል፡፡

ስለጉዳዩ የማሪታይም ጉዳዮች ባለሥልጣንን ለማነጋገር ሪፖርተር ያደረገው ጥረት ሊሳካ አልቻለም፡፡ 

Standard (Image)

ማኅበራዊ የጤና መድን ተቀልብሶ በሌላ ሊተካ እንደሚችል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጠቆመ

$
0
0

አዋጅ ወጥቶለትና መዋቅር ተዘጋጅቶለት በሁሉም የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ተግባራዊ ሊደረግ የነበረው ማኅበራዊ የጤና መድን ሥራ ላይ እንዳይውል እክሎች እንደገጠሙት፣ በዚህም ምክንያት በሌላ አሠራር ሊተካ እንደሚችል የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ለፓርላማው ይፋ አደረጉ፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሠራርና የአባላት ሥነ ምግባር ደንቡ መሠረት ሚኒስትሮችን በመጥራት በሚመለከታቸው ጉዳዮች ላይ የመጠየቅ መብት ያለው ሲሆን፣ ይህንኑ መሠረት በማድረግም ከተሾሙ የሁለት ወራት ዕድሜ ብቻ ያስቆጠሩትን የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩን ፕሮፌሰር ይፍሩ ብርሃነን ሐሙስ ታኅሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ጠርቷል፡፡

የፓርላማው አባላት ለሚኒስትሩ ካቀረቧቸው ጥያቄዎች መካከል፣ በአገሪቱ እየተዘረጉ የሚገኙ የጤና መድን ሥርዓቶች ያሉበት ደረጃን የተመለከተው ጥያቄ ይገኝበታል፡፡

ማኅበራዊ የጤና መድን ሥርዓትን ለመዘርጋት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አዋጅ ወጥቶ ወደ ወደ ሥራ በመግባት የመጨረሻ ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበር ያስታወሱት ሚኒስትሩ፣ በኅብረተሰቡ ዘንድ ያለው አናሳ ግንዛቤና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች እንቅፋት እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡

የጤና መድን አዋጅ ቁጥር 690/2010 ፀድቆ በኋላም ማሻሻያ የተደረገበት መሆኑ ይታወቃል፡፡ የጤና መድን ሽፋን ዋናው ዓላማም ሁሉን አቀፍ የሆነ የጤና ሽፋንን ለማረጋገጥ በመንግሥትና በተጠቃሚው ኅብረተሰብ መካከል ወጪን መጋራት መሆኑን አዋጁ ይጠቅሳል፡፡

በመሆኑም ሁሉም የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችና የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን በመጀመሪያ ተጠቃሚ የማድረግ ዓላማ ወጥኖ ነበር፡፡ ወደ ትግበራ ለመግባትም የመንግሥት ሠራተኞች ወርኃዊ መዋጮ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው፣ መንግሥትም የራሱን ድርሻና ለጡረታ ባለመብቶች ተጨማሪ መዋጮ የማድረግ ግዴታ ተቀምጦለት ብሔራዊ የጤና መድን ኤጀንሲም ተቋቁሞ ነበር፡፡

‹‹የማኅበራዊ ጤና መድንን ወደ ትግበራ ለማስገባት ያልተቻለው በቂ ቅድመ ዝግጅት ስላልተደረገለት ነው፤›› ሲሉ ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ የሠራተኞች ግንዛቤ አናሳ ስለሆነና ብዙ ጥያቄዎችን ሊያስነሳ የሚችል በመሆኑ፣ እንዲሁም ከመድኃኒት አቅርቦትና ከጤና ተቋማት ተደራሽነት ጋር ብዙ መሠራት ያለባቸው ጉዳዮች በመኖራቸው ወደ ትግበራ እንዳይገባ መወሰኑን ገልጸዋል፡፡

‹‹ምናልባትም ሌላ አማራጭ ልንከተልና ይኼኛው አሠራር እንዲቀር ልንወስን እንችላለን፤›› ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የባለሙያዎች ቡድን በዚህ አዲስ አማራጭ ላይ ጥናት እያደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

ሌላኛው የጤና መድን አሠራር ማኅበረሰብ አቀፍ የጤና መድን ሲሆን፣ ውጤታማ ስኬቶችን እያስመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ ወደ 18 ሚሊዮን ወይም 18 በመቶ የሚሆነውን የኅብረተሰብ ክፍል መሸፈን እንደቻለ ገልጸዋል፡፡

በ364 ወረዳዎች የተዘረጋው ይህ ሥርዓት ማኅበረሰቡ በጤና መድህን በማሳተፍ ከ800 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ በጤናው ዘርፍ አስቸጋሪ ከሆኑ ጉዳዮች አንዱ የመድኃኒት አቅርቦት መሆኑን ሚኒስትሩ አምነዋል፡፡ የመድኃኒት አቅርቦቱን የሚያከናውነው የመድኃኒት ፈንድ አቅርቦት ኤጀንሲ መሆኑን የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ ‹‹ይህንን ተቋም የግድ ማዘመን ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡

መድኃኒት ለመግዛት በዓመት 150 ጊዜ ጨረታ የሚያወጣ ድርጅት መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የመድኃኒት አቅርቦት ድርጅቶችን በመምረጥ አብሮ እየሠራ አለመሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍ የረዥም ጊዜ የአቅርቦት ማዕቀፍ ስምምነት ከታዋቂ ድርጅቶች ጋር ለመፍጠር እንደሚሠሩ፣ መድኃኒት አገር ውስጥ ከገባበት ጊዜ አንስቶ ተጠቃሚዎች ዘንድ እስኪደርስ ድረስ ኮምፒዩተራይዝድ በሆነ ሥርዓት ቁጥጥር የሚደረግበት ሥርዓት ለመዘርጋት ጥረት ላይ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

Standard (Image)

ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግና ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን በ16 ሚሊዮን ብር ዕዳ ተከሰሱ

$
0
0

የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የጉምሩክና የኢኮኖሚ ወንጀል ዳይሬክቶሬትንና የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንን ከውጭ አገር በሕጋዊ መንገድ የገባ የአርማታ ብረት ያላግባብ መውሰዳቸው በፍርድ ቤት በመረጋገጡ፣ ከ16 ሚሊዮን ብር በላይ ዕዳ እንዲከፍሉ በአስመጪው ድርጀት የክስ አቤቱታ ቀረበባቸው፡፡

ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀጥታ ክስ ፍትሐ ብሔር ችሎት በሁለቱ የመንግሥት ተቋማት ላይ የክስ አቤቱታ ያቀረበው፣ ወሪ ጄኔራል ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ነው፡፡

ማኅበሩ በክስ አቤቱታው እንደገለጸው፣ ከውጭ አገር ብረት አስመጪ ከሆኑ ድርጅቶች ላይ በመግዛት ዓለም ገና በሚገኘው መጋዘኑ ያከማቻል፡፡ በተለይ ትኩረት አድርጎ የሚገዛቸው የአርማታ ብረቶችን በመሆኑ ‹‹የአርማታ ብረቶች ችርቻሮ ንግድ›› የሚባል የችርቻሮ መሸጫ ሱቅ ተክለሃይማኖት አካባቢ በመክፈት እየነገደ መሆኑን ለችሎቱ አስረድቷል፡፡

ማኅበሩ የዕለት ተዕለት ሥራውን በማከናወን ላይ እያለ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሚያዚያ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. ዓለም ገና በሚገኘው መጋዘኑ በመሄድ፣ 670,460 ኪሎ ግራም (670.46 ሜትሪክ ቶን) የአርማታ ብረት በሕገወጥ መንገድ የገባ መሆኑን በመግለጽ እንደወሰደበት በአቤቱታው አመልክቷል፡፡ በወቅቱ በነበረው የአንድ ኪሎ አርማታ ብረት ዋጋ 24 ብር መሆኑን የጠቀሰው ማኅበሩ፣ ወለዱንና ላለፉት አራት ዓመታት እየናረ የመጣውን የዋጋ ግሽበት ሳይጨምር የ670.46 ሜትሪክ ቶን ብረት ዋጋ 16,091,040 ብር መሆኑንም ጠቁሟል፡፡

ባለሥልጣኑ ከማኅበሩ ብረቶቹን የወሰደው መሐመድ ከድር አብዲ የተባለ ግለሰብ ከቀረጥና ግብር ነፃ መብት ተጠቅሞ በሕገወጥ መንገድ ያስገባው በማስመሰል ቢሆንም፣ ብረቶቹ በማኅበሩ መጋዘን ውስጥ የተከማቹት በምን ሁኔታ እንደሆነ የሚያረጋግጥ ሰነድም ሆነ ማስረጃ ሳይኖር እንደሆነ ማኅበሩ በክስ አቤቱታው አስረድቷል፡፡

ብረቶቹ የተከማቹት በሕገወጥ መንገድ ከውጭ አገር በማስገባት ነው ቢባል እንኳን፣ በወቅቱ ድርጊቱን የማጣራት ሥልጣን የነበረው የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሆኖ ሳለ፣ ባለሥልጣኑ ‹‹ውክልና አለኝ›› በማለት የፈጸመው ድርጊት ትክክል እንዳልነበር ማኅበሩ በአቤቱታው አስታውቋል፡፡

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የአርማታ ብረቶቹ በሕገወጥ መንገድ የገቡ መሆናቸውንና መንግሥትም ሊያገኝ ይገባ የነበረውን የተጨማሪ እሴት ታክስና የግብር ክፍያዎች ማጣቱን በመግለጽ በመዝገብ ቁጥር 165434 ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የክስ አቤቱታ ያቀረበ ቢሆንም፣ ፍርድ ቤቱ ጥቅምት 8 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰጠው ብይን ማኅበሩ ብረቶቹን በመጋዘኑ ያከማቸው በሕጋዊ መንገድ ከአስመጪዎች በመግዛት መሆኑን ከቀረቡለት ሰነዶችና ምስክሮች ማረጋገጡን ገልጾ፣ የቀረበውን የወንጀል ክስ ውድቅ ማድረጉን ማኅበሩ ባቀረበው የክስ አቤቱታ ላይ ገልጿል፡፡

ከሳሽ ወሪ ጄኔራል ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የተወሰደበት የአርማታ ብረት ያላግባብ መሆኑን በፍርድ ቤት ጭምር ያረጋገጠ መሆኑን በመግለጽ፣ የአርማታ ብረቱ በተወሰደበት ጊዜ ባለው ዋጋ ሳይሆን አሁን በወቅታዊው ዋጋ ተሰልቶ በገንዘብ ከነወለዱ፣ ወይም ብረቱ በወቅቱ በነበረው ዋጋ ተሰልቶና ብረቱንና የዋጋውን ልዩነት ገንዘብ ከነወለዱ እንዲከፈለው ለጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የጉምሩክና ኢኮኖሚ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ጥያቅ ያቀረበ ቢሆንም፣ ሊቀበለው እንዳልቻለ በክስ አቤቱታው ገልጿል፡፡

በመሆኑም የክስ አቤቱታው የቀረበለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀጥታ ክስ ፍትሐ ብሔር ችሎት፣ ማኅበሩ ያቀረበለትን የክስ አቤቱታ ተመልክቶ ክፍያው እንዲፈጸምለት ትዕዛዝ እንዲሰጥለት አመልክቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ የቀረበለትን የክስ አቤቱታ ተመልክቶ ሁለቱ የመንግሥት ተቋማት የካቲት 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ቀርበው እንዲያስረዱ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡ 

Standard (Image)

ገበያውን ዘግይቶ የተቀላቀለው ዘቢዳር ቢራ በጣት የሚከፈት የጠርሙስ ቢራ አቀረበ

$
0
0

በ1.2 ቢሊዮን ብር ኢንቨስትመንት በቤልጂየሙ ዩኒብራና በጀማር ሁለገብ ኢንዱስትሪ ኩባንያዎች አክሲዮን ድርሻ የተቋቋመው ዘቢዳር ቢራ አክሲዮን ማኅበር፣ ለቢራ ኢንዱስትሪው አዲስ የሆነና የጠርሙስ መክፈቻ ሳያስፈልገው በጣት የሚከፈት ቢራ ለገበያ አቀረበ፡፡ ዘቢዳር ቢራ ሐሙስ ታኅሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. በገበያ ላይ ያዋለው ቢራ በደቡብ ክልል፣ ከአዲስ አበባ በደቡብ ምዕራብ በኩል 167 ኪሎ ሜትር ርቃ፣ ከወሊቂጤ ከተማ አቅራቢያ በምትገኘው ጉብርየ ተብላ በምትጠራው መንደር ውስጥ የተጠመቀ ነው፡፡ ቢራው ለገበያ መቅረቡን በማስመልከት በጎልፍ ክለብ ቅጥር ግቢ ውስጥ በተከናወነ ሥነ ሥርዓት ላይ፣ አንድ ሺሕ ያህል ሰዎች የተሳተፉበት በቢራ ቅርፅ የተዘጋጀ የሰዎች ትዕይትንም ተከናውኗል፡፡ ይህ ትዕይንት በጊነስ የድንቃ ድንቅ መዝገብ ላይ ሊሰፍር እንደሚችል ይገመታል፡፡ መጠሪያውን በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን ውስጥ ከሚገኘው የዘቢዳር ማሲፍ ተራራ የተዋሰው ዘቢዳር ቢራ፣ በ150 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የተገነባ ፋብሪካው በዓመት 350 ሺሕ ሔክቶ ሊትር የማምረት አቅም እንዳለው የቢራ ፋብሪካው ኃላፊዎች ገልጸዋል፡፡ ዝርዝር ዘገባውን በቢዝነስና ኢኮኖሚ ገጽ ላይ ይመልከቱ፡፡

 

Standard (Image)

ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን በእነ አቶ መላኩ ፈንታ ጉዳይ ፍርድ ቤት ተጠርቶ ተጠየቀ

$
0
0

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን በእነ አቶ መላኩ ፈንታ የክስ ጉዳይ ተጨማሪ ማስረጃ እንዲያቀርብ ፍርድ ቤት በተደጋጋሚ ያስተላለፈውን ትዕዛዝ፣ በአግባቡ ለምን እንዳልፈጸመ ማክሰኞ ጥር 2 ቀን 2009 ዓ.ም. ኃላፊዎች ቀርበው ተጠየቀ፡፡

የእነ አቶ መላኩ ፈንታን የክስ መዝገብ ቁጥር 14/356 በመመርመር ላይ የሚገኘው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት፣ በመዝገቡ ላይ ተገቢውን ፍትሕ ለመስጠት በአራት ተከሳሾች ድርጅቶች ላይ ባለሥልጣኑ ማስረጃ እንዲልክለት በተደጋጋሚ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡

የአቶ ነጋ ገብረ እግዝአብሔር ድርጅት ነፃ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ የአቶ ከተማ ከበደ ድርጅት ኬኬ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ የአቶ ገብረ ሥላሴ ገብሬ ድርጅት ኮሜት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበርና አቶ ጌቱ ገለቴ በሥራ አስኪያጅነት የሚመሩት ጌትአስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ናቸው፡፡

ድርጅቶቹ ከ2003 ዓ.ም. እስከ 2005 ዓ.ም. ድረስ ከሚሌ እስከ አቃቂ ቃሊቲ ላጋር ጉምሩክ የፍተሻ ቦታዎች ድረስ የተመረጡ ዕቃዎችን ሲያጓጉዙ፣ ተገቢውን ግብር መክፈላቸውን ወይም ካልከፈሉ በመንግሥትና ሕዝብ ገቢ ላይ ያደረሱትን ጉዳት ገልጾ እንዲልክ ነበር ትዕዛዝ የተላለፈለት፡፡

ፍርድ ቤቱ በላከው ትዕዛዝ መሠረት ባለሥልጣኑ ኅዳር 15 ቀን 2009 ዓ.ም አራቱም ድርጅቶች የተሰጣቸውን የግብር ከፋይ መለያ ቁጥር፣ በሚሌ ጉምሩክ በኩል በተደረገው ማጣራትና ፍተሻ ተስተናግዶ የተገኘ የጉምሩክ ዲክላራሲዮን መረጃ በሲስተም ውስጥ እንዳልተገኘ ጠቅሶ ምላሽ ሰጥቶ ነበር፡፡ ነገር ግን ፍርድ ቤቱ በድጋሚ በሰጠው ትዕዛዝ እንደገና ተፈትሾና አጣርቶ ተገቢው ምላሽ እንዲልክለት ሲጠይቅ፣ ባለሥልጣኑ በሁሉም ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች ድርጅቶቹ ለበርካታ ዓመታት የከፈሉትን የቀረጥና የግብር ክፍያዎችን እየመረመረ መሆኑንና የጨረሱትን አያይዞ ምላሽ በመስጠት፣ ለቀሪዎቹ ተጨማሪ ጊዜ ጠይቋል፡፡

ተከሳሾቹ በተደጋጋሚ ባቀረቡት ተቃውሞ ዓቃቤ ሕግ በክሱ አካቶ ያላቀረበውን ፍርድ ቤቱ በተጨማሪ ማስረጃነት መጠየቅ እንደሌለበት፣ ችግሩ አለ ቢባል ባልተከራከሩበት ጉዳይ እንዴት ብይን ሊሰጥ እንደሚችል፣ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ነው ቢባል እንኳን በግልጽ የተጠየቀው ከሚሌ እስከ መዳረሻ ባሉ ፍተሻ ቦታዎች፣ በተደረገ የጭነት ልክ ቀረጥና ታክስ መክፈል አለመክፈሉን አረጋግጦ እንዲልክ እንጂ፣ ለበርካታ ዓመታት የሠሩበትን አለመሆኑን አስረድተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ በመጨረሻ ባስተላለፈው ትዕዛዝ የተቋሙ ኃላፊ ቀርበው እንዲያስረዱ በማለቱ፣ የገቢዎችና ጉምሩክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነብዩ ሳሙኤል ቀርበው አስረድተዋል፡፡

በፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መሠረት ለምን እንዳላኩ ተጠይቀው፣ የተረዱት በፍርድ ቤት እንደተነገራቸው ሳይሆን አጠቃላይ እንቅስቃሴውን እንደመሰላቸው ገልጸው በቀጣይ በትዕዛዙ መሠረት እንደሚፈጸም አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም ባለሥልጣኑ በፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መሠረት በስምንት ቀናት ውስጥ ምላሽ እንደሚሰጥ ትዕዛዝ ሰጥቶ፣ በመዝገቡ ላይ ብይን ለመስጠት ለጥር 15 ቀን 2009 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

 

Standard (Image)

የውጭ ኩባንያዎች በስኳር ፕሮጀክቶች ለመሳተፍ ፍላጎት አሳዩ

$
0
0

- ኮርፖሬሽኑ ዘንድሮ ከውጭ ስኳር አላስገባም ብሏል

ለረዥም ዓመታት የተጓተቱና ከተያዘላቸው በጀት በላይ የበሉ ስኳር ፕሮጀክቶችን ለመታደግ፣ መንግሥት በሽርክና መሥራት ለሚፈልጉ ኩባንያዎች ባቀረበው ግብዣ በርካታ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ፍላጎታቸውን አሳዩ፡፡

ከአፍሪካ፣ ከአውሮፓና ከሩቅ ምሥራቅ አገሮች የመጡ በርካታ ኩባንያዎች ከመንግሥት ጋር በሽርክና ኢንቨስት ለማድረግ ጥያቄ እያቀረቡ፣ የመግባቢያ ሰነድ እየተፈራረሙና ዝርዝር ጥናቶችንም ማካሄድ መጀመራቸውን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የኩባንያዎቹን ጥያቄ ለማስተናገድ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የኢንቨስትመንት ጥናትና ልማት ዘርፍ ኮሚቴ አዋቅሮ እየሠራ እንደሚገኝም ተገልጿል፡፡ ይኼ ኮሚቴ  የኩባንያዎቹን ምክረ ሐሳብ ከመረመረ በኋላ በኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ አብተው ለሚመራው የስኳር ኮርፖሬሽኑ ሥራ አመራር ቦርድ አቅርቦ እንደሚያስወስን ታውቋል፡፡ ቦርዱ ካፀደቀውና የኩባንያዎቹ ጥያቄ ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች ሚኒስትር ዴኤታ አቶ በየነ ገብረ መስቀል ቀርቦ ይሁንታ ካገኘ ወደ ሥራ ይገባል ተብሏል፡፡

በውስብስብ ችግሮች ውስጥ የተዘፈቀው የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ካለበት ችግር ውስጥ ለማውጣት፣ በአገር ውስጥና በውጭ ኢንቨስተሮች ላይ ትኩረት ተደርጓል፡፡ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ፍላጎት ያላቸው የአገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎች ወደ ዘርፉ እንዲገቡና በስኳር ልማት እንዲሳተፉ ጋብዟል፡፡

ኮርፖሬሽኑ በነባር ስኳር ፋብሪካዎችና በተጀመሩ አሥር የስኳር ፋብሪካ ፕሮጀክቶች በተለይ በስኳር ልማት፣ በኢታኖል ልማት፣ በመሠረተ ልማት ዝርጋታ፣ በመሬት ልማት፣ በቤቶች ግንባታ መስኮች ኢንቨስት ማድረግ ለሚፈልጉ ኩባንያዎች ግብዣ ማድረጉን አስታውቋል፡፡

ኮርፖሬሽኑ በተለይ በኢታኖል ልማት ራሳቸውን ችለው ለሚያለሙ ኩባንያዎች በሩን ክፍት ማድረጉንም ጨምሮ ገልጿል፡፡ ፍላጎት ያላቸው ኩባንያዎች በቂ ካፒታል፣ የዕውቀት ሽግግር ማድረግ የሚችሉ፣ የገበያ ትስስር ያላቸው መሆንም እንዳለባቸው ኮርፖሬሽኑ ባወጣው የፍላጎት መግለጫ ላይ አስታውቋል፡፡

የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን በነባሮቹ መተሐራ፣ ፊንጫና ወንጂ ሸዋ ስኳር ፋብሪካዎች የማስፋፊያ ፕሮጀክቶች አካሂዷል፡፡ ተንዳሆን ጨምሮ 11 አዳዲስ ስኳር ፕሮጀክቶችም በመካሄድ ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ አዳዲስ ስኳር ፕሮጀክቶች በኮንትራት አስተዳደርና በፋይናንስ ዕጦት ውስጥ እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ኮሙዩኒኬሽን ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጋሻው አይችሉህም ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ እነዚህን ፕሮጀክቶች ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ኮርፖሬሽኑ የአሠራር ለውጥ አድርጓል፡፡ ‹‹የአሠራር ለውጡ ኩባንያዎቹ ከመንግሥት ጋር በጋራ ሠርተው የትርፍ ተካፋይ እንዲሆኑ በማድረግ በዘርፉ ለውጥ ማምጣት፤›› ነው ሲሉ አቶ ጋሻው ተናግረዋል፡፡

ነገር ግን በተለይ ወደ ምርት ያልገቡት ስኳር ፋብሪካዎች ከአገር ውስጥና ከውጭ ከ70 ቢሊዮን ብር በላይ የተበደሩ ቢሆንም፣ ፕሮጀክቶች በሥራ አፈጻጸም ችግር ከመዘግየታቸው ባለፈ የብድር መክፈያ ጊዜያቸው የቀረበ መሆኑ እየተገለጸ ነው፡፡

ከአገር ውስጥ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ፣ ከውጭ ደግሞ  የህንድና የቻይና ባንኮች ለፕሮጀክቶቹ ብድር ካቀረቡት መካከል ይገኙበታል፡፡ በሼባ ቦንድ ተጨማሪ ገንዘብ ማግኘቱም ይታወሳል፡፡

ተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ በ1997 ዓ.ም. ሲጀመር 64 ሺሕ ሔክታር መሬት ለማልማት 26 ሺሕ ሜትሪክ ቶን  ስኳር እንደሚያመርት፣ ይኼ ፕሮጀክትም በሦስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ዕቅድ ተይዞ ነበር፡፡

የተንዳሆ ብድር የተገኘው ከህንድ እንደመሆኑ ግንባታውም ኦቨርሲስ ኢንፍራስትራክቸር አልያንስ ለተሰኘ የህንድ ኩባንያ ተሰጥቶ ነበር፡፡

ነገር ግን ተንዳሆ ከተያዘለት ጊዜ እጅግ ዘግይቶ ከ12 ዓመታት በኋላ ቢጠናቀቅም፣ ማምረት ግን አልጀመረም፡፡ ይህ ፕሮጀክት ግድቡ ብቻ በ1.8 ቢሊዮን ብር ይጠናቀቃል ተብሎ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ እስካሁን 5.6 ቢሊዮን ብር እንደወጣበት ተገልጿል፡፡

ሌሎችም ፕሮጀክቶች ይጠናቀቃሉ ተብሎ በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ መጠናቀቅ ካለመቻላቸውም በላይ፣ ከተያዘላቸው በጀት በላይ እየወጣባቸው መሆኑ እየተገለጸ ነው፡፡

ኮርፖሬሽኑ እነዚህን ፕሮጀክቶች ለማጠናቀቅ የግድ የውጭና የአገር ውስጥ ኢንቨስተሮች ተሳትፎ እንደሚፈልግ ተገልጿል፡፡

ከአገር ውስጥ ኩባንያዎች ውስጥ አሁን ባለው ሒደት አሚባራ ግብርና ልማት ኩባንያ ተሳታፊ ሆኗል፡፡ አሚባራ በስድስት ሺሕ ሔክታር መሬት ላይ ሸንኮራ አገዳ አልምቶ ለከሰም ስኳር ፋብሪካ ማቅረብ መጀመሩን አቶ ጋሻው ገልጸዋል፡፡

ስኳር ኮርፖሬሽን በተያዘው በጀት ዓመት ከውጭ ስኳር ሳያስገባ ለመጀመሪያ ጊዜ በአገር ውስጥ ለመሸፈን ማቀዱን አቶ ጋሻው ተናግረዋል፡፡ ከነባሮቹ በተጨማሪ አርጆ ደዴሳ፣ በብረታ ብረትና ኢንጅነሪግ ኮርፖሬሽን የሚገነባው ኩራዝ ቁጥር አንድና በቻይናው ኮምፕላንት የሚገነባው ኩራዝ ቁጥር ሁለት ስኳር ፋብሪካዎች ወደ ምርት ይገባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ አስረድተዋል፡፡

ከእነዚህ አዳዲስ ፋብሪካዎችና ከነባሮቹ በአጠቃላይ ሰባት ሚሊዮን ኩንታል ስኳር ይመረታል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ይህም ለአገር ውስጥ ፍጆታ በቂ በመሆኑ የአገር ውስጥ ፍላጎት በአገር ውስጥ ምርት ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሚሸፈን አቶ ጋሻው ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን ባለፈው በጀት ዓመት የተገዛው 1.5 ሚሊዮን ኩንታል ስኳር ወደ አገር በመግባት ላይ መሆኑን የሚናገሩት አቶ ጋሻው፣ ይህ ስኳር መጠባበቂያ ይሆናልም ብለዋል፡፡

Standard (Image)
Viewing all 1275 articles
Browse latest View live