በአገሪቱ ለተፈጠረው ችግር መፍትሔው ከእኛ ብቻ ነው በሚል መንፈስ ከመንግሥትም ሆነ ከገዥው ፓርቲ የተሰጠውን አቅጣጫ አጥብቆ እንደሚኮንን፣ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) አስታወቀ፡፡ መንግሥት መፍትሔ ከእኔ ብቻ ነው የሚገኘው ብሎ በግትርነት የሚጓዝ ከሆነ፣ የአገሪቱን ችግሮች ከማባባስ የዘለለ ፋይዳ እንደማይኖረውም ኢዴፓ አስታውቋል፡፡
ኢዴፓ ይህን ያስታወቀው፣ ‹‹የገዥው ፓርቲና የመንግሥት ግምገማ የአገሪቱን ችግር በጥልቀት ያልፈተሸ ነው፤›› በማለት ማክሰኞ ጳጉሜን 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ነው፡፡
‹‹ገዥው ፓርቲና መንግሥት እንደሚሉት የችግሩ ምክንያት ከዕድገታችን ጋር ተያይዞ የሕዝቡ የመጠየቅ ባህል ማደግ፣ የአመራሩ በሥልጣን መባለግ፣ ወዘተ ብቻ አይደለም፡፡ ዋነኛው የችግሩ ምንጭ መንግሥት የፖለቲካ ምኅዳሩን ከማጥበቡ የመጣ፣ ሕዝቡ በተወካዮቹ አማካይነት ችግሮቹንና ብሶቶቹን ሊያሰማባቸው የሚችልባቸውን በተለያየ እርከን ላይ ያሉ የሕዝብ ምክር ቤቶችን ከስግብግብነት በመነጨ ጠቅልሎ በመያዙ ነው፤›› በማለት ኢዴፓ አሁን የተፈጠረውን ችግር መንስዔ አስቀምጧል፡፡
ኢዴፓ ሰላማዊ ሠልፍ የማድረግም ሆነ የመሰብሰብ መብት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሸራረፈ ከመሄዱም በላይ ሰላማዊ ሠልፍ ለማድረግ ወደማይቻልበት ደረጃ መደረሱ፣ የፖለቲካ ሙስና መስፋፋቱ፣ የፌዴራል ሥርዓቱ ከአንድነት ይልቅ ለልዩነት ዕድል የሚሰጥ መሆኑና በአጠቃላይ የዴሞክራሲያዊና የሰብዓዊ መብቶች መጣስ ሌላው የችግሮች መንስዔ ናቸው በማለት ይገልጻል፡፡
በዚህም መሠረት አሁን በከፍተኛ አመራሩ የግምገማ ውጤት ለችግሩ መፈጠር መነሻ ተብለው የቀረቡ ምክንያቶች የሥርዓቱ ችግሮች መሆናቸውን ኢዴፓ እንደሚያምን ገልጿል፡፡
ከዚህ አንፃር መንግሥትና ገዥው ፓርቲ የሕዝቡን ሰላምና ደኅንነት የሚያስጠብቅ ዘላቂ መፍትሔ ከማስቀመጥና ሰፊ የሕዝብ መድረክ ፈጥሮ ግጭቱን በውይይት የሚፈታበትን አቅጣጫ ከማስቀመጥ ይልቅ፣ ችግሩን በፀጥታ ኃይሉ ጣልቃ ገብነት ብቻ ለመፍታት መወሰኑ ተገቢ እንዳልሆነ ኢዴፓ አስታውቋል፡፡
‹‹መንግሥት እየወሰደው ያለው ውሳኔና ዕርምጃ ችግሩን የሚያባብስ እንጂ ዘላቂ መረጋጋት የማያመጣ ነው፤›› በማለት አስታውቆ፣ ‹‹የሚወሰደው ዕርምጃም ሕዝቡን ቁጣ ውስጥ በመክተት ለከፍተኛ ደም መፋሰስ እንዳይዳርግ፤›› በማለት ፓርቲው ያለውን ሥጋት ገልጿል፡፡
በመሆኑም መንግሥት ለችግሩ መፍትሔ ከእሱ ብቻ የሚመነጭ አድርጎ ማሰቡንና አሁንም በፀጥታ ኃይሉ ጣልቃ ገብነት ብቻ ችግሩን ለመፍታት አቅጣጫ ማስመቀጡን፣ ኢዴፓ አጥብቆ እንደሚያወግዝ አስታውቋል፡፡
በተጨማሪም ሕዝብ ችግሮቹንና ብሶቶቹን መጠየቅና ማሰማት ዴሞክራሲያዊ መብቱ መሆኑን ፓርቲው እንደሚያምን ገልጾ፣ ነገር ግን የሚያደርገውን ተቃውሞ ፍፁም ሰላማዊና ሕጋዊ በማድረግ፣ ጨዋነቱን ጠብቆ ከሌላው የኅብረተሰብ ክፍል ጋር ለዘመናት የቆየውን የመቻቻል፣ የመከባበርና የአብሮነት ባህሉን ከሚጎዱ ማንኛውም ዓይነት ድርጊቶች እንዲቆጠብ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
ኢዴፓ በተቀሰቀሱት ግጭቶች የጠፋውን የሰው ሕይወት፣ የአካል መጉደል፣ የንብረት ውድመትና የሰብዓዊ መብት ረገጣን የሚያጣራ ገለልተኛ አጣሪ ኮሚቴ ተቋቁሞ በአስቸኳይ ውጤቱ ለሕዝብ ይፋ እንዲሆን ጠይቋል፡፡
